Monday 6 June 2016

የኖርዲክ ሃገራት ለአርበኞች ግንቦት ሰባት 2.42 ሚሊዮን ብር ለገሱ!!



በትላንትናዉ ለት 04/06/2016 በኖርዌይ ኦስሎ ከተማ በስካንዲክ ሃገራት የሚኖሩ የአርበኞች ግንቦት 7 አባላት ግብረሃይል አስተባባሪነት የአርበኞች ግንቦት 7 ለፍትህ፣ ለዲሞክራሲና፣ ለነፃነት በተደረገዉ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት 800 ሺ የኖርዌጅያን ገንዘብ (2.42 ሚሊዮን ብር) ገቢ ተሰበሰበ። በዕለቱ ዝግጅት ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ከኤርትራ ግንባር እንዲሁም ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ኃይሌ በክብር እንግድነት የተገኙ ሲሆን የግንቦት 7 አመራር የነበረዉና በኢትዮጵያ መንግስት ከየመን ታፍኖ የተወሰደዉ አቶ አንድአርጋቸዉ ፅጌ እህት ወ/ሮ ብዙአየሁ ፅጌ ባልተጠበቀ ሁኔታ ከቦታዉ መገኘት ታዳሚዉን ከፍተኛ ስሜት ዉስጥ የከተተ ነበረ። በተለይም ወ/ሮ ብዙአየሁ በቦታዉ ላይ በመገኘት ያደረጉት ንግግርና ያቀረቡት ግጥም ታዳሚዉን በስሜት የናጠና አብዛኛዉን የእልህ እንባ ያስነባ ነበረ። የገቢ ማሰባሰብያዉን ዝግጅት ለመሳተፍ ከስዊድን የመጡ የድርጅቱ አባሎችና ደጋፊዎች ያቀረቡት በዝሙሮችና ጭፈራዎች የታዳሚዉን ቀልብ የሳቡ ነበሩ።

በዝግጅቱ መጀመሪያ ወደ መድረክ የተጋበዙት የስዊድን የአርበኞች ግንቦት 7 ሥራ አስፈፃሚ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ዘለሌ ሲሆኑ ለዝግጅቱ መሳካት የስዊድን ሥራ አስፍፃሚ አመራር ከኖርዌይ ግብረሃይል ጋር በመተባበር በጥምረት እንደሰሩት ገለፃ ያደረጉ ሲሆን አያይዘዉም በስዊድን ስቶክሆልም ለኢሳት ገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ላይ በተደረገዉ የስነፅሁፍ ዉድድር አሸናፊ በመሆን የሜዳሊያ ተሸላሚ የሆነዉ ወጣት ሜዳሊያዉን በኤርትራና በኢትዮጵያ ድንበር ለሀገራቸዉ ነፃነት ለሚታገሉ አርበኞች በስጦታነት እንዲረከብለት በአደራ የላከዉን የሜዳሊያ ሽልማት ለፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ አስረክበዋል። በመቀጠል ወደመድረኩ የተጋበዙት ለፕሮፌሰር ጌታችዉ እስካሁን በኢትዮጵያዉስጥ ያለዉ አፈናና የኢኮኖሚ ዉድቀት ሂደት አደገኛና አስጊ ሁኔታ ዉስጥ መሆኑን በመግለፅ የወያኔን ስርዓት ማስወገድ አማራጭ የሌለዉ መፍትሄ መሆኑና በአሁን ሰዓት አርበኞች ግንቦት 7 እያደረገ ያለዉ ስልታዊ ትግል ትክክለኛ መፍትሄ መሆኑን በመግለፅ ሆሉም ኢትዮጵያዊ ይህንን ሃገርን የማዳን ጥሪ በመቀበል ወደ ትግበራ እንዲያመራ ጥሪያቸዉን አስተላልፈዋል በማያያዝም በኦሮሚያ እየተካሄደ ያለዉ ሕዝባዊ አንቢተኝነት የወያኔ አስከፊና ቅጥ የለሺ አገዛዝ ዉጤት መሆኑን በመግለፅ በአፀፋዉ ወያኔ አየወሰደ ያለዉን ኢሰብአዊ የኃይል እርምጃ ኮንነዋል የኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ እንደሚያካትትም አያይዘዉ ገልፀዋል።

በመቀጠል ወደመድረክ የተጋበዙት በጉጉት ሲጠበቁ የነበሩት ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ባደረጉት ንግግር በሚያደርጉት የትግል ሂደት ዉስጥ እንደ ፕሮፌሰር ጌታቸዉ አይነት ሰዉ ያለዉን የሞያና የእዉቀት ግብአት መሰረታዊ መሆናቸዉን ገልፀዉ የአርበኞች ግንቦት 7 ለፍትህ፣ ለዲሞክራሲና፣ ለነፃነት እየተከተለ ያለዉ የትግል ስርዓት የደቡብ አፍሪካ ጥቁሮች የአፓርታይድ ስርዓትን ለመደምሰስ የሄዱበት መንገድን እንደሚከተል በመግለፅ የአፓርታይድ ሰርዓት አሁን በኢትዮጵያ ካለዉ አገዛዝ ጋር የሚመሳሰልበትን ነጥቦች በመዘረዘር በጥልቀት ለታዳሚዉ አስረድተዋል በመቀጠልም የትግል ስልቱ ከዉጪ ሃገራት በሚደረግለት ተፋሰስ የሚደጎምና በዛ ላይ መሰረት ያደረገ ሳይሆን ከእያንዳንዱ ሃገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ በሚደርግ ድጋፍ ትግሉ የዉጤት በር ድረስ የሚቀጥል መሆኑንም አበክረዉ ተናግረዋል አያይዘዉም ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከአስከፊዉ የወያኔ ስርዓት በቶሎ ለመላቀቅ ከመቸዉም ግዜ በበለጠ መልኩ አብዝቶና አምርሮ እንዲታገል ጥሪአቸዉን አቅርበዋል።

የምግብ እረፍት በመስጠት የተጀመረዉ የጨረታ ዝግጅት ከፍተኛ ፉክክር የተካሄደበት ሲሆን ነዋሪነታቸዉን በኖርዌይ በርገን ከተማ ያደረጉ አርበኞች ከስዊድን የግንባሩ አባላት ጋር ያደረጉት ፉክክር ቀልብን የሳበ ነበረ፤ በመቀጠልም ኢካደፍ(ኢትዮጵያን ከረንት አፌርስ)በኩል ጨረታዉን ለመዉሰድ የተደረገዉ ዉድድር እጅግ በጣም አስደሳች የነበረ ሲሆን ሌላዉ ማህበረሰብም የነበረዉ ተሳትፎ እጅግ የሚያኮራ ነበረ በስተመጨረሻም የአቶ አንድአርጋቸዉ ፅጌ እህት ወ/ሮ ብዙአየሁ ፅጌ ለጨረታ የቀረበዉን ምስል በ ከፍተኛዉን ገንዘብ በግለሰብ በመክፈል በማሸነፍ ሽልማቱን ለኖርዌይ የአርበኞች ግንቦት 7 አባላት ያበረከቱ ሲሆን የኖርዌይ የአርበኞች ግንቦት 7 ተወካይ ስእሉን ለስዊድን ግንቦት 7 አባላት በስጦታነት አስረክበዋል።

በስተመጨርሻም ዝግጅቱ ሰፋ ላለ የዉይይት መድረክ ክፍት በማደረግ በዝግጅቱ ላይ የታደሙት ማህበረሰቦች ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ጋር በአርበኞች ግንቦት 7 ለፍትህ ለዲሞክራሲና ለነፃነት የትግል ስርዓትና ሂደት በዝርዝር በመወያየት ዝግጅቱ ተጠናቋል።


0 comments:

Post a Comment