Wednesday 7 September 2016

በኦሮሚያ የተለያዩ ከተሞች ያለመገበያየትና ቤት ውስጥ የመቀመጥ አድማው በተሳካ ሁኔታ ለ2ኛ ቀን እየተደረገ ነው

እስከመስከረም 2 ይቆያል የተባለውና በኦሮሚያ ከትናንት ጀምሮ በተለያዩ ከተሞች እየተደረገ ያለው ከቤት ያለመውጣት እና ያለመገበያየት አድማ በተሳካ ሁኔታ እየተደረገ መሆኑ ተሰማ::

በሐረርጌ ዳዳር ከተማ ሱቆችና ትናንስፖርት ሙሉ በሙሉ ሥራ ያቆሙ ሲሆን አንዳችም የዓመት በዓል ገበያ የለም:: በከተማዋ አልፎ አልፎ ውር ውር ከሚሉ የፖሊስ መኪኖች ውጭ ምንም ነገር የለም:: ፖሊሶች ሕዝቡ ሱቁን እንዲከፍት ለማስፈራራት ቢሞክሩም ሕዝቡ ግን በቆራጥነቱ እንደቀጠለ ነው::

በምስራቅ ሐረርጌ ቆቦም እንዲሁ ምንም ዓይነት የንግድ እንቅስቃሴ ቆሞ ሕዝብ ቤት ተቀምጦ አድማውን በተሳካ ሁኔታ እያደረገ ይገኛል::

በኮፋሌምም ሙሉ በሙሉ ንግድና ትራንስፖርት መቆሙን ከአካባቢው የሚመጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ:: በአሳሳ፣ በሳርቦ ጅማ፣ በነቀምቴ ሕዝባዊ እምቢተኝነቱና የሥራ ማቆም አድማው የቀጠለ ሲሆን በተለይም በሌሎች የጅማ ከተሞች የባጃጅ ማቆሚያ ቦታዎች በአጋዚ ጦር ተከበዋል:: በከተማዋ የትራንስፖርት እጥረት በመከሰቱ አጋዚዎቹ በግዳጅ ባጃጅ ሹፌሮቹ እንዲጭኑ በማስገደድ ላይ እንደሆነ መረጃዎች ደርሰውናል::

በኦሮሚያ የተጀመረውና 2ኛ ቀኑን የያዘው ያለመገበያየትና ቤት ውስጥ የመቀመጥ አድማ በአርሲ አዳባ፣በባሌ ሮቤ፣ በጉደር፣ በቡራዩ፣ በሱሉልታ በም ዕራብ ሽዋና ሌሎችም ከተሞች ቀጥሎ ገበያ የሚባል የለም::

0 comments:

Post a Comment