Thursday 15 September 2016

ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በባለቤቱ ሲታወስ

ጋዜጠኛና ጦማሪ እስክንድር ነጋ በፌደራል አቃቤ ህግ ከሳሽነት የሽብር ክስ ተከሶ ያለዋስትና በፍርድቤት ትዕዛዝ ታስሮ ከዛም የእስራት ፍርድ ተፈርዶበት እስር ቤት ከገባ መስከረም 3 ቀን 2009 ዓ.ም አምስት አመታት ሆኖታል፡፡ ድፍን አምስት አመታትን አዲስ አበባ በሚገኘው የፌደራል ማረሚያቤት ቃሊቲ በእስራት ሲያሳልፍ የስራ ባልደረባው፣ ባለቤቱ እንዲሁም የልጁ እናት ጋዜጠኛ ሰርክዓለም ፋሲል አመታቱን ከልጇ ናፍቆት እስክንድር ጋር ከቃሊቲ አሁን በስደት እስካሉበት አሜሪካን አገር ድረስ ያለፉበትን መንገድ ትናገራለች፡

2004 ዓ.ም
መስከረም ገና ከመጥባቱ በሶስተኛው ቀን ነበር እስክንድር በፖሊሶች ተይዞ ወደ የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ በተለምዶ ማዕከላዊ ወደተባለው ፖሊስ ጣቢያ የተወሰደው፡፡ "ልጁ ናፍቆት ለመጀመሪያ ጊዜ ወደትምህርት ቤት የሄደበት ቀን ነበር፡፡ እስክንድር ከትምህርት ቤት ናፍቆትን ሲያመጣው የማዕከላዊ ፖሊሶች እጁን በካቴና አስረው ወደ መኪና ሲያሰገቡት ሰላየ በበነጋታው 'እኔንም ፖሊሶቹ ይወሰዱኛል ብሎ ረበሸን' የትምህርት ቤት በር ላይ ፖሊሶች እንደሚጠበቁት ሰላሰበ ለሳምንታት ትምህርት ቤት ሳይሄድ አሳለፈ፡፡"

ህገመንግሰታዊ መብቱ ተጥሶ በማዕከላዊ ያለምንም የጠበቃ የሃይማኖት አባት እና ቤተሰብ ግንኙነት መስከረም እና ጥቅምት 2004 ዓ.ም በማዕከላዊ ምርመራ አሳልፏል፡፡ "አንትን ማሰር ሰልችቶናል" የሚል ማስፈራሪያ በተደጋጋሚ ይደርሰው የነበረው እስክንድር ማዕከላዊ በነበረበት ወቅት ምንም አይነት መረጃ ስላለበት ሁኔታ ማወቅ አልተቻለም ነበር፡፡ "በድብቅ ከመደበኛ የፍርድ ቤት የስራ ሰዓት ውጪ በጊዜ ቀጠሮ ፍርድቤት ይቀርቡ ነበር፡፡ ሁለቱ ወራት አስቸጋሪ እና የሰቀቀን ቀናቶች ነበሩ፡፡"

ከማዕከላዊ የምርመራ ቆይታ በኃላ "የተከሰሰው በሽብር ክስ ሰለነበር ተጨማሪ ድንጋጤ ሆኖብኝ ነበር፡፡ እስክንድር በፃፈው ቢከሰስ አይቆጨኝም ነበር፡፡ ባልሰራው እና ባላደረገው መከሰሱ ያናድዳል"

2005 ዓ.ም
በታሰረበት ዓመት እጅግ በፈጣን የፍርድቤት የክርክር ሂደት በ2004 ዓ.ም በሰኔ 20 ቀን የ18 ዓመት ፅኑ እስራት የተፈረደበት እስክንድር አዲሱን አመት 2005ዓ.ም የጀመረው ለፌደራል ጠቅላይ ፍርድቤት ይገባኝ ሰሚ ችሎት የከፍተኛው ፍርድቤትን ውሳኔ እንዲሽርለት ይግባኝ ማመልከቻውን አስገብቶ ነበር፡፡

"እስክንድር ላይ የመሰከረው የአቃቤ ህግ ብቸኛ የሰው ምስክር አቶ ዘመኑ ሞላ፣ በሚመሰክሩበት ወቅት ያለተናገሩትን እና ያላሉትን ነገር፤ ከምስክር ቃል ያለተወስደ በመቅረፀ ድምፁ ውስጥም የሌለ በምስክር የወረቀት ግልባጭ ላይ እንደሰፈረ ጠቅላይ ፍርድቤትም የምስክሮችን ኦርጀናል የድምፅ ቅጂ ሰምቶ ይግባኙን እንዲያይ ተከራክሮ ነበር "
"ብዕር ላነሳ አስራ ስምንት አመት እጅግ ከባድ ነው" የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የከፍተኛው ፍርድቤት እስክንድር ላይ የፈረደውን የአስራ ስምንት አመት እስራት ውሳኔ እንድፀና ወስኗል በዚሁ 2005 ዓ.ም

ሰርክዓለም በእስክንድር እስር ሁለት ነገር ይሰማኛል ትላለች፡-
1.እፎይታ፡- ከመታሰሩ በፊት የትም ይሂድ የት፣ ከማንም ጋር ያውራ፣ ምንም ያድርግ ከአጠገቡ የመንግስት ደህንነት ሰራተኞች ይከተሉታል፡፡ ያሰፈራሩታል፡፡እርሱ ያገኛቸውን ሰዎች ሁሉ ያሰፈራራሉ፣ ያዋክባሉ፡፡ እንደው ድንገት በወጣበት የሆነ ነገር አድርገውት እንዳይቀር የዘወትር ሰጋቴ እና ሰቀቀኔ ነበር፡፡ አሰረው ሰላሰቀመጡት ከስጋት ከሰቀቀን እና ከፍርሃት እፎይታ አግኝቻለሁ፡፡

2.ቁጭት፡- እስክንድር ለሃገሩ መስራት የፈልጋል፡፡ እሱም የበኩሉን አስተዋፅኦ ማበርከት የዘወትር ህልሙ ነው፡፡መንግስትም ከእስክንድር ትችቶች መማር ሲችል በካቴና አስሮ እስር ቤት መወርወሩ ያሰቆጨኛል፡፡

2006ዓ.ም
ፍርድቤት ከፈረደበት ፍርድ ይልቅ እስክንድር እራሱ ላይ ታላቅ ፍርድ የፈረደበት ዓመት ነው ትላለች ሰርክዓለም፡፡ "እፎይ ብዬ ልታሰርበት፡፡ እስሬ የብቻዬ ነው” ብሎ ልጁን፣ ቤተሰቡን ዳግም ላለማየት ሲወስን እስክንድር በአላማው ፅኑ መሆኑን ያረጋገጠበት አመት ነበር"
አርፌ መታሰር እፈልጋለሁ፡፡ እናንተን እያሰብኩ እንዲሁም ችግር መከራችሁን እያየሁ ሁለት እስር መታሰር አልፈልግም ብሎ ሲለኝ በውስጡ ያለው እልህ የእነርሱን ጭካኔ አሳይቶኝ ነበር፡፡ የመከራውን ፅዋ ለብቻው መጠጣት ነው የፈለገው ትላለች ባለቤቱ ሰርክዓለም አንባ በሚተናነቅው ሳግ ባዘለ ድምፅ፡፡

2007ዓ.ም
ስደት በአሜሪካ፡፡ ናፍቆት ትምህርት ቤት ጀመረ፡፡ ስርክ ዓለም በአሜሪካን ሃገር የመኖሪያ ፈቃድ ለማውጣት መወሰኗ በፊት እናቴን እንዴት እንደሆነ ጠይቂልኝ አልኳት ትላለች፡፡ "እፎይ ብዬ አሁን ተኛሁ፡፡ ሃሳብ ከላዬ ወርዶ በሠላም እንቅልፍ እተኛለሁ ብሎ ላከብኝ"
አሁን ባለችበት አሜሪካ ከልጇ ጋር ስትምጣ ምንም አይነት የባይተዋር ሰሜት እንዳለተሰማት እያሰታወሰች ስደትን ሳይታወቀን እንድኗሪ ለመድነው ትላለች፡፡

2008 ዓ.ም
"የሚጎል ነገር እንዳለ እያወቅን ኑሮ ጀመርን፣ የባዶነት ህይወት "

2009ዓ.ም
ተስፋ
"ተሰፋዬ የእስክንድር ይፈታል አይደለም፡፡ ተስፋዬ እስክንድር ለአመታት እስር የተዳረገበት፣ የተንገላታለት፣ ቤተሰቡን ሁሉን መሰዋዕት አድርጎ የታሰረለት ሐሳብን የመግለፅ ነፃነት ተከብሮ ማየት ነው፡፡ ሐሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ሲከበር ያኔ እስክንድርም ይፈታል፡፡ አለበለዚያ እስክንድር ከእስር ቢፈታ እንኳን ዳግም ይታሰራል፡፡"

0 comments:

Post a Comment