Saturday 2 July 2016

በናይሮቢ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የረሀብ አድማ አደረጉ

በኬንያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞችና የፖለቲካ ፓርቲ አባላት ሀብታሙ አያሌው እገዳው ተነስቶለት የውጪ ህክምና እንዲያግኝ በናይሮቢ-አምነስቲ ቢሮ ፊትለፊት በረሀብ አድማ ጥያቄ ሲያቀርቡ ዋሉ። ሥርዓቱ በፈጠረባቸው ጫና ለስደት የተዳረጉት እነኚህ ጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች በቀድመው አንድነት ፓርቲ አመራር በሀብታሙ አያሌው ምስል የተሰራ ቲሸርት በመልበስ ፤በቀድሞው አንድነት ፓርቲ አመራር በሀብታሙ አያሌው ላይ የተጣለበት የፍርድ ቤት እግድ እንዲነሳና በውጪ ሀገር ተገቢውን ህክምና እንዲያገኝ የሰብዓዊ መብት ተቋሙ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ግፊት እንዲያደርግ ጠይቀዋል።

ሀሳባቸውን በነጻ በመግለጻቸውና ሙያቸውን ተግባራዊ በማድረጋቸው ሳቢያ በአገዛዙ አለስቃይና እንግልት የተዳረጉ በርካታ ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች ወደ ኬንያ ኡጋንዳና ወደሌሎች የተለያዩ ሀገራት ተሰደው በችግርና በስጋት እንደሚገኙ ይታወቃል። 

በረሀብ አድማ ላይ ሆነው በናይሮቢ የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ጽህፈት ቤት በመገኘት ጥያቄ ሲያቀርቡ የዋሉት እነኚህ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የሀብታሙ አያሌው ህይወት ላይ የከፋ አደጋ እንዳይደርስ ያደረባቸውን ስጋት በመግለጽ እንደ ሀብታሙ ሁሉ በተለያዩ እስር ቤቶች እየተገረፉና በህመም እየተሰቃዩ ያሉ የህሊና እስረኞች እንዲለቀቁና ተገቢውን ህክምና እንዲያገኙ ተማጽነዋል። ኢትዮጵያውያን የማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ትናንት እና ዛሬ ሐብታሙ አያሌው የጉዙ እግዱ ተነስቶለት በውጪ ሀገር ህክምና እንዲያገኝ በዘመቻ መልክ እየጠየቁ ይገኛሉ። 

ዓለማቀፉ የሰብዓዊ መብት ተቋም አምነስቲ ኢንተርናሽናል በበኩሉ በዚሁ ጉዳይ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማፘም ደሳለኝ ደብዳቤ እንደጻፈ ትናንት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።


0 comments:

Post a Comment