Saturday 22 November 2014

እኔም ሃና ነኝ ( ሄኖክ የሺጥላ )


unnamed 
ሀና ላይ በተፈጠረው ነገር እጅግ አዝኛለሁ ፣ ሃና ላይ የደረሰው ነገር ሀገሬ ላይ እየደረሰ ያለውን ነገር እንዳስታውስ ነው ያረገኝ ። ሃናስ ታክሲ ውስጥ ነው የተደፈረችው ፣ ሀገሬ ግን በየጎዳናው ፣ ህገ ወጥ በሆነ የመሬት ንግድ ፣ ህገ ወጥ በሆነ እስር ፣ ህገ ወጥ በሆኑ ሕጋዊ ሌቦች ፣  ህገ ወጥ በሆነ ዶዘር ፣ ህገ ወጥ በሆነ ዱርዬ ቡድን እዚም እዛም ( ጭኑዋም ተረከዙዋም ፣ እጁዋም ወገቡዋም  ተደፍሮዋል ) ።
 
እንድ ነገር ለማከል ብዙ ሰዎች ” እኔም ሀና ነኝ ” ማለት ጀምረዋል ፣ ያዝልቅላችሁ ፣ ታዲያ በነካ እኔነታችሁ ” እኔም ራሴ እኔ ነኝ !” በሉኝ ።  ክርስቶስ  ተመልሶ ቢመጣ ” ሰው ራሱን ሳይሆን ሌላ ሰው መሆን እንደምን ይቻለው ይሆን ?” ብሎ ያስተምር ነበር ። ለነገሩ ድጋሚ ክርስቶስ መጥቶ ለኛ ቢሰቀል፣ ለምን ተሰቀለ ብለን ከስቅለቱ እና ከደሙ ተምሳሌተ ትምህርት በመውሰድ ፈንታ ” እኔም ክርስቶስ ነኝ !” የምንል ይመስለኛል ። ከቻልን ያልሆነውን  አንሁን ፣ ወይ ደሞ ነን ስንል ሆነን  ብቻ ከሆነ ይሁን ።
 
አንድ ጥያቄ አለኝ ።  የሃና ጉዳይ ያገባኛል ያሉ ድህረ ገጾች ” የሀገሬ ጉዳይ ያገባኛል ማለት እንዴት ተሳናቸው ?” በሃና ስቃይ የተቆጡ እና ያነቡ አይኖች እንዴት ስለ  ህጻን ነብዩ ለመናገር ፈሩ ?  ሀና ፍትህ ያስፈልጋታል ያሉ አንደበቶች  እንዴት የሽብሬ ወይም የ በቀለ ገርባ ወይም የእስክንድር መታሰር  ብሎም የእስሩ ኢ ፍትሃዊነት አልታይ አላቸው ? ከሀናነት በፊት እንዴት ራሳቸው ፍትህ እንደሚያስፈልጋቸው መጠየቅ አቃታቸው ። ሃናን ነኝ ስንልስ ምን ማለታችን ነው ? ሃና ላይ የደረሰው እኔ ላይ እንደደረሰ ያህል ነው ማለት መሰለኝ ? ይደለም ? ከሆነ ዘንዳ ታዲያ  “ታላቁ” ( በትምህርተ ጥቅስ ውስጥ ይሁን ታላቁ  የሚለው ቃል )  አዎ ታላቁ  የገነት ሰይጣን ክርስቶስን ” እስኪ ይሄን ድንጋይ ዳቦ አድርገው?” ሲለው ክስቶስ ” ሰው በእሕል ብቻ እንደማይኖር ! ” ያስረዳዋል ! እኔ ከክርቶስ የተማርኩት ይህንን ነው፣  ነጻነት እኔም አከሌን  ነኝ  በማለት አይገኝም ፣ በመሆን ብቻ !!! አንዳንድ ሰዎች ከክርስቶስ ተማርን ብለው የሚሉት ስለ ገነት ማሰብን ነው ። ሰው ሆይ አጠገብህ ያለውን ገሀነም የሙጥኝ ብለህ እንዴት ስለ ገነት ታወራልህ ? ሰው ሆይ ለኢትዮጵያም እንደ ሃና  እንጮኸላት ዘንድ ኢትዮጵያስ  ሀገርህ ታክሲ ውስጥ ትደፈር ወይ ? አደጋ የማያደርስብንን ነገር ብቻ እየመረጥን የነጻነት እና የመብት ተሙዋጋች መምሰል ማስመሰሉን እናቁም ። አዎ የሃና ቁስል ፣ በተደፈረችበት ሰዓት ያሰማችው ጩኸት ፣ የፈሰሰው ደሟ ሁሉም ያማል ፣ ያስቆጫል ፣ ያበሳጫል ። ግን ታዲያ እኮ  ፍትህ ላንድ ሰው ከተጉዋደለ ለሁሉም እንደተጉዋደለ ነው ። እኔ ሃናን ነኝ ስትል ” በእውነት ግን ነኝ ወይ  ብለህ ራስህን  ለመጠየቅ አንድ ሰከንድ ይኑርህ ” እኔ ክርስቲያን ነኝ ስትልም እንዲሁ ፣ እኔ ሙስሊም ነኝ ስትልም እንዲሁ ። እያሳሰበን ያለው የፍትህ መጉዋደል ሳይሆን የተጉዋደለው ፍትህ ለመጮህ ይመቻል ወይስ አይመችም የሚለው ስለመሰለኝ ነው ። አጠገብህ ያለውን ወንድምህን ሳትወድ እኔን ያላየከውን እንዴት ልትወድስ ትችላለህ ያለው አሁንም  ክርስቶስ ነው ! በ ፌስ ቡክ ገጾቻችን ላይ የለጠፍናት ሃና አሁን የኢትዮጵያ ሕዝብ ያለበትን የ ሞራል ውድቀት እና የስርዓቱን ዋልጌነት ያሳያል ብላችሁ መቼም ተሯሩጣችሁ እንደማታነሱት ነው፣ የሃና ደም የስርዓቱ ጭፍግግ የሞራል ድቀት ያፈሰሰው ድንግልና ነው፣ ሃና የተደፈረችው ሳትወለድ ነው ፣ ሃና የተደፈርችው የዛሬ 23 ዓመት ነው ፣ ሃና ክብሩዋ የተዋረደው ፣ ጭኑዋ በጉልበት የተፈለቀቀው ዛሬ አይደለም ፣ ትናንት ነው ፣ አጉራ ዘለል ፣ ጥራዝ ነጠቅ ፣ እና ቦዘኔ ስርዓት እና መሪ ኢትዮጵያን መምራት የጀመሩ ቀን ነው ፣ የሃና ቀሚስ የላላው ። የሃና እናት መቀነት የተፈታው ፣ በ ሬዲዮና በቴሌቪዥን ሕዝቡን የሚሳደብ መሪ የተፈጠረ ለት ነው ፣ ሃና ከተደፈረች ቆይታለች ። ሃናን የሚደፍር ስብእና ያለው ትውልድ ሲፈጠር ፣ እንደዛ አይነት ትውልድ ኮትኩቶ ያሳደገ ስርዓት ሲፈጠር ሃና ተደፍራለች ።  ዛሬ ብዙ ሀናዎች ታስረዋል ፣ ብዙ ሃናዎች ተገድለዋል ፣ ብዙ ሃናዎች ገና ይታሰራሉ። ወይንሸት ማን መሰለች ሃና እኮ ነች ፣ ርዮት ማን መሰለች ሃና ራሷ ነች ። እና ሃና  ነን ስንል   የሚያሳስር እና የማያሳስር እየመረጥን ሳይሆን የሆነውን እና የሆ—ነውን መሆን አለበት ። ነጻነታችንን ካላስመለስን ሀገር ሃና ትሆናለች መርዎቹዋ ደፍሪዎቹዋ !!!!
 
አትርሱት  ሕዝብ በቁጥርም በመንፈስም ከመንግስት ይበልጣል ስለዚህ   ሕዝብ ከቆረጠ  ያሸንፋል ። ጊዜ የመከራ መለኪያ ቁና ቢሆን እንጂ ያለመቻላችን መገለጫ አይሆንም ! እንበርታ !!!! ከ ጨቁዋኞቹ ሳይሆን ከተጨቁዋኞቹ ጎን መቆም ነው ሃናነት ፣ ሀናነት ትግል ነው ፣ እምቢ ማለት ነው ፣ ውስጡ ሞት ቢኖርበትም !  እኔ ሃናን ነኝ ስንል ፣ በሞት ጥላ ስር እንኩዋ ብሄድ ሞትን አልፈራም ብሎ ማለት ነው ።  አንድ ወዳጄ እንዳለው ”  ኢትዮጵያና ህዝቦቿ ተደፍሯል! ዴሞክራስ፣ መልካም አሥተዳደር፣ ፍትህ፣ ነፃ ምርጭ እና የህግ የበላይነት ያልተከበረበት አገር አገርቷም ህዝቧም በግዳጅ የተደፍሩ ናቸው።”

0 comments:

Post a Comment