Sunday 23 August 2015

ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በድጋሜ የሰማያዊ ሊቀመንበር ሆነው ተመረጡ

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

አንደኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ለሁለት ቀናት በአዲስ አበባ ያደረገው ሰማያዊ ፓርቲ ኢ/ር ይልቃል ጌትነትን በድጋሜ የፓርቲው ሊቀመንበር አድርጎ መርጧል፡፡

ትናንት ነሀሴ 16/2007 ዓ.ም ጉባኤውን የጀመረው ፓርቲው በዛሬው ሁለተኛና የማጠቃለያ ውሎው የፓርቲውን ሊቀመንበር፣ የብሄራዊ ምክር ቤት አባላት እንዲሁም የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን አባላት ምርጫን አድርጓል፡፡


ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በድጋሜ ለቀጣዩ ሦስት አመታት ፓርቲውን እንዲመሩ የተመረጡ ሲሆን፣ አምስት የኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን አባላትም በጉባኤው ተመርጠዋል፡፡ ጉባኤው የፓርቲውን የብሄራዊ ምክር ቤት አባላትንም መርጧል፡፡ 


ለፓርቲው ሊቀመንበርነት ቀደም ብለው ፓርቲውን ለሁለተኛ ዙር ለመምራት ራሳቸውን በእጩነት ያቀረቡት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ብቻ ሲሆኑ፣ ጉባኤው ተጨማሪ እጩዎችን ለመቀበል ባቀረበው ሀሳብ መሰረት ራሱን በእጩነት የሚያቀርብ ይኖራል ተብሎ ቢጠበቅም በእጩነት ራሱን ያቀረበ አልነበረም፡፡ 


በመሆኑም በፓርቲው ህገ ደንብ መሰረት ጉባኤው ተጨማሪ እጩዎችን በጥቆማ ለማወዳደር ተገድዷል፡፡ በዚህም ጉባኤው ስድስት እጩዎችን የጠቆመ ቢሆንም አምስቱ ‹‹አንወዳደርም›› በማለታቸው ከተጠቆሙት መካከል አቶ ዮናታን ተስፋዬ ብቻ ለመወዳደር ፍላጎታቸውን ገልጸዋል፡፡ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ፓርቲውን በህዝብ ግንኙነት ማገልገላቸው የሚታወስ ሲሆን ዛሬ ደግሞ ለሊቀመንበርነት መወዳደር ችለዋል፡፡ 


ለሊቀመንበርነት እጩ ሆነው የቀረቡት ሁለቱ እጩዎች በጉባኤው ፊት በተመደበላቸው ጊዜ ገደብ ውስጥ ራሳቸውን ካስተዋወቁና የምረጡኝ ቅስቀሳ ካደረጉ በኋላ ወደ ድምጽ መስጠት መግባት ተችሏል፡፡ በተሰጠው ድምጽ መሰረትም ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰማያዊ ፓርቲን ለቀጣይ ሦስት አመታት እንዲመሩ በአብላጫ ድምጽ ተመርጠዋል፤ በዚህም ኢ/ር ይልቃል ከተሰጠው ድምጽ 136 ድምጽ አግኝተው ሲያሸንፉ፣ አቶ ዮናታን ተስፋዬ በበኩላቸው 60 ድምጽ በማግኘት ፉክክር አድርገዋል፡፡ 


የምርጫ ውጤቱ ይፋ መሆኑን ተከትሎ ንግግር ያደረጉት ተመራጩ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰማያዊ ፓርቲ በሁለቱ ቀናት ጉባኤው ያነሳቸውን ችግሮች ለመፍታት እንደሚሰሩ ገልጸዋል፡፡ 


የሰማያዊ ፓርቲ ጠቅላላ ጉባኤ በዛሬው ውሎው ቀጣይ የፓርቲውን እንቅስቃሴ አስመልክቶም በጉባኤው አባላት አጠቃላይ ውይይት አድርጓል፡፡ በዚህም ፓርቲው ወደፊት ማደራጀት ላይ አተኩሮ መስራት እንደሚገባው ጉባኤው አጽንኦት ሰጥቶበታል፡፡
ጠቅላላ ጉባኤው የብሄራዊ ምክር ቤትና የፓርቲው ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን ያቀረቡት ሪፖርት ላይ ተወያይቶ ሪፖርቶቹ የፓርቲው ሰነድ ሆነው እንዲፀድቁ በአብላጫ ድምፅ ወስኗል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ለሁለት ተከታታይ ቀናት ያካሄደውን ጉባኤ ዛሬ ነሀሴ 17/2007 ዓ.ም አጠናቅቋል፡፡


Thursday 20 August 2015

ፍርድ ቤቱ አራቱ ፖለቲከኞች ነፃ እንዲለቀቁ ወሰነ




ዛሬ ነሃሴ 14/2007 ዓ.ም የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት በዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የተከሰሱትን 2ኛ ተከሳሽ ሀምታሙ አያሌው፣ 3ኛ ተከሳሽ ዳኤል ሽበሽ፣ 4ኛ ተከሳሽ አብርሃ ደስታና 5ኛ ተከሳሽ የሸዋስ አሰፋ እንዲሁም 7ኛ ተከሳሽ አብሃም ሰለሞን በነፃ እንዲለቀቁ ወስኗል፡፡ 


በአንፃሩ አንደኛ ተከሳሽ ዘላለም ወርቃገኘሁ ከአሁን ቀደም ተከሶበት በነበረውና ከ15 አመት በላይ እንደሚያሳስር የሚታወቀው የፀረ ሽብር ህጉ አንቀፅ አራት ‹‹ማሴር፣ ማቀድ ተግባረት›› ላይ መረጃ ስላልተገኘበት አንቀፁ ወደ 7/1 ላይ በተመለከተው ላይ ተቀይሮ እንዲከላከል ተበይኖበታል፡፡ በዚህ አንቀፅ ለግንቦት ሰባት በመመልመል ተግባር ተሰማርቷል በሚል እንደተከሰሰም ተገልጾአል፡፡ በተመሳሳይ 6ኛ፣ 8ኛ፣ 9ኛ ፣10ኛ ተከሳሾች ከአንደኛ ተከሳሽ ጋር እንዲከላከሉ ተብለዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ አራቱ ፖለቲከኞች ሲታሰሩ በኢግዚቢት የተያዘባቸው ተለቆላቸው እንዲፈቱ ሲወንስ እንዲከላከሉ ያላቸው የመከላከያ ምስክር እንዲያስመዘግቡ በይኗል፡፡

Wednesday 19 August 2015

የዛሬው የዞን 9 ጦማሪያን የፍርድ ቤት ውሎ

በሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ ሶልያና ሽመልስ (በሌለችበት) በፍቃዱ ኃይሉ፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አጥናፍ ብርሃኔ እና አቤል ዋበላ በዛሬው ዕለት ‹ክሳቸውን መከላከል ያስፈልጋቸዋል ወይስ አያስፈልጋቸውም› በሚል የመጨረሻ ውሳኔውን ለመስማት በፍርድ ቤት ተገኝተው ነበር፡፡

በዕለቱ የተሰየመው ችሎት ‹‹ሰነዱ ሰፊ ነው ብዙ ማንበብ ይጠይቃል በዚህም ምክንያት ችሎቱ የክስ መዝገቡን አይቶ ባለመጨረሱ ለመጪው ሰኞ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል» በማለት ቀጠሮው መተላለፉ በዳኛው የተነገረ ቢሆንም የፀረ ሽብር ክሶችን የሚያየው 19ኛ ወንጀል ችሎት ነሃሴ 15 ቀን ይዘጋል ተብሎ አስቀድሞ በዳኞች ተነግሮ የነበረ ቢሆንም ግልፅ ባልሆነ ሁኔታ ለነሃሴ 18 የብይን ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል።

481 ቀናትን በእስር ያሳለፉት ጦማሪያን የሚቀጥለው ቀጠሮአቸው 35ኛው ይሆናል ፡፡ በዕለቱ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ታሳሪዎች በመገኘታቸው የጦማሪያኑ ቤተሰቦች እና ወዳጆች፣ ጋዜጠኞች እና የዲፕሎማቲክ ኮሚኒቲ አባላት ችሎቱን እንዳይታደሙ ተከልክለዋል፡፡

Tuesday 18 August 2015

እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ ግንቦት 7ን ለመቀላቀል መንቀሳቀሳቸውን አመኑ

እነ ብርሃኑ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጡ
‹‹ድርጊቱን ፈጽመናል፣ ጥፋተኞች ግን አይደለንም››
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

 
ከግራ ወደ ቀኝ – ፍቅረማርያም አስማማው፣ ብርሃኑ ተክለያሬድ እና እየሩሳሌም ተስፋው
የኢትዮ-ኤርትራ ድንበርን በማቋረጥ ኤርትራ ከሚገኘው ግንቦት ሰባት የተባለ በተወካዮች ምክር ቤት ሽብርተኛ ተብሎ ከተፈረጀ የሽብር ቡድን ጋር ለመቀላቀል ሲጓዙ ድንበር አካባቢ ማይካድራ ላይ እንደተያዙ በመግለጽ በመንግስት የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው እነ ብርሃኑ ተክለያሬድ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጡ፡፡

ዛሬ ነሐሴ 11/2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ እየሩሳሌም ተስፋው፣ ፍቅረማርያም አስማማውና ደሴ ካህሳይ ‹‹በክሱ ላይ የተመለከተውን የወንጀል ድርጊት ፈጽመዋል ወይስ አልፈጸሙም›› የሚል ጥያቄ ከፍርድ ቤቱ እየተነሳላቸው፣ በየተራ የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡ በዚህም አራቱም ተከሳሾች ድርጊቱን እንደፈጸሙ በመግለጽ፣ ነገር ግን ጥፋተኛ አለመሆናቸውን አስረድተዋል፡፡


አንደኛ ተከሳሽ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ‹‹ሀገሬ በፋሽስት አምባገነኖች ተይዛ ዜጎች በጨቋኝ ስርዓት ውስጥ ስላሉ ሀገሬንና ህዝቤን ነጻ ለማውጣት ወጣትነቴን ሰውቼ ለመታገል ግንቦት ሰባት ከሚባል ነጻ አውጭ ድርጅት ጋር ለመቀላቀል ወስኜ ወደዚያው አቅንቻለሁ፡፡ ስለዚህ ድርጊቱን ፈጽሜያለሁ፣ የግንቦት ሰባት አባል ነኝ፡፡ ወንጀለኛ ግን አይደለሁም›› ሲል ቃሉን ለፍርድ ቤቱ ሰጥቷል፡፡ ሁለተኛ ተከሳሽ እየሩሳሌም ተስፋው በበኩሏ፣ ‹‹ድርጊቱን ፈጽሜያለሁ፤ ነገር ግን ጥፋተኛ አይደለሁም›› ብላለች፡፡


ሦስተኛ ተከሳሽ ፍቅረማርያም አስማማው ደግሞ፣ ‹‹ህገ-መንግስቱን አምኜ በሰላማዊ ትግል ውስጥ ስሳተፍ የደረሰብኝን አውቃለሁ፡፡ ሰላማዊ ትግል እንደማያዋጣም ተረድቻለሁ፡፡ በዚህ ሰዓት ኢትዮጵያ ውስጥ ዴሞክራሲን ለመገንባት የሚያስፈልገው የነጻነት ትግል ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ግንቦት ሰባት ነጻ አውጭን ለመቀላቀል ስጓዝ ማይካድራ ላይ ተይዣለሁ፡፡ ስለዚህ ድርጊቱን ፈጽሜያለሁ፤ ጥፋተኛ ግን አይደለሁም›› ብሏል ለችሎቱ፡፡


አራተኛ ተከሳሽ ደሴ ካህሳይ በበኩሉ፣ ‹‹አርሶ አደር ነኝ፣ ሰሊጥ አመርታለሁ፡፡ ነገር ግን ያመረትሁትን ሰሊጥ የኢህአዴግ ወታደሮች ይዘርፉኛል፤ መስራት አልቻልኩም፡፡ በዚህ ምክንያት ሌላ ስራ መስራት ስላልቻልኩ የኢትዮጵያ አርበኞች ግንባርን ተቀላቅያለሁ፡፡ ለዚህ ግን ጥፋተኛ አይደለሁም›› ሲል የእምነት ክህደት ቃሉን ሰጥቷል፡፡


ፍርድ ቤቱ የተከሳሾችን ቃል ካዳመጠ በኋላ የአቃቤ ህግን አስተያየት የጠየቀ ሲሆን፣ አቃቤ ህግ ተከሳሾች ጥፋተኝነታቸውን ስላላመኑ ማስረጃ እንዲያቀርብና እንዲያሰማ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡ ስለሆነም ፍርድ ቤቱ የአቃቤ ህግ ማስረጃን ለመስማት ለነሐሴ 22/2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡



Sunday 16 August 2015

“አንገነጠልም – ትግላችን የኦሮሞ ሕዝብ ውሳኔ ተግባራዊ እንዲሆን ማድረግ ነው” ብ/ ጀነራል ኃይሉ ጎንፋ ከአስመራ

ከሁለት ሳምንት በፊት አራት የኦነግ ድርጅቶች ወደ አንድ መምጣታቸውን ይህን ተከትሎ ከአውስትራሊያ የሚሰራጨው ሲቢኤስ ራድዮ ብ/ጄ ኃይሉ ጎንፋ፤ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር – ኦነግ (በአባ ነጋ ጃራ የሚመራው) ምክትል ሊቀ መንበር፤ ስለ ኦነግ ዳግም መሰባሰብ አነጋግሯቸዋል:: ጄነራሉ ተበታትነን ምንም አናመጣም ብለዋል:: “ኦነግ የሚለውን ስያሜ በባለቤትነት እኔ ነኝ ብሎ የሚወስደው ማን ነው?” ለሚለው ጥያቄም ምላሽ ሰጥተዋል:: ያድምጡት::

Thursday 13 August 2015

የኤልያስ ገብሩ ቆይታ ከጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ጋር (ዝዋይ እስር ቤት)

በኤልያስ ገብሩ
  • ታገሉ! ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ (ከዝዋይ እስር ቤት)
  • ተመስገን ደሳለኝ ስለሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ፍርድም ሀሳቡን ሰንዝሯል
Temesgen Desalegn Fteh newspaper editor
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ

ቦሌ አካባቢ ብርዱ ጠንከር ያለ ነበር፡፡ ከቦሌ ብራስ ወደሚሊኒየም አዳራሽ በሚወስደው ቀጭን መንገድ ላይ ወንዱም ሴቱም በፍጥነት ይራመዳል፡፡ ከታክሲ በሁለቱም አቅጣጫዎች የወረዱ ሰዎች ወደመደበኛ ሥራቸው ለመግባት ብሎም የግል ጉዳያቸውን ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ ነበር – ከትናንት በስትያ ሰኞ (ነሐሴ 04 ቀን 2007 ዓ.ም) ጥዋት 1፡45 ሰዓት፡፡

እኔ እና ወዳጄ አቤል ዓለማየሁ ወደከአዲስ አበባ 160 ኪሎ ሜትር ርቀት ወደሚገኘው ዝዋይ እስር ቤት አምርተን ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬን እና ተመስገን ደሳለኝን ለመጠየቅ በዚህ ቀን ቀጠሮ ይዘን ነበር፡፡ አቤል ከቀጠሯችን 20 ደቂቃ ዘግይቶ፣ ቦሌ ጫፍ ደረሰና ወደቃሊቲ መናሃሪያ ሁለት ታክሲዎችን በመጠቀም ደረስን፡፡ ወደዝዋይ የሚጭኑ ሚኒባስ ታክሲዎች እና ‹‹አባዱላ/ዶልፊን›› የሚል መጠሪያ የተቸራቸው የህዝብ ማመላለሻ መኪኖች ቢኖሩም በተለምዶ ‹‹ቅጥቅጥ›› የሚባለውን መካከለኛ አውቶቡስ ምርጫችን አደረግን – የትራፊክ አደጋን በመስጋት፡፡

የተሳፈርንበት አውቶቡስ፣ ከቃሊቲ ትንሽ ወጣ ካለ በኋላ፤ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም፣ በእስር ላይ የሚገኙትን የግንቦት 7 ዋና ፀሐፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ “ልማቱን አሳዩኝ” ሲለን ከከተማ ወጣ እያደረግን የምነሳየው… [እውነት ግን፣ በከባድ እስር ላይ መሆናቸው የሚገመተው አቶ አንዳርጋቸው ‹ልማቱን አሳዩኝ› ይሏቸዋልን?!]›› ሲሉ ለቪኦኤዋ ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸው የገለጹትን፣ የአዲስ አበባ አዳማ አዲሱ የፍጥነት መንገድ (Express way)ን ተቀላቀለ፡፡ በዚህ መንገድ ሁለታችንም ሄደን አናውቅም ነበር፡፡ ሆኖም እስከዛሬ ካየኋቸው የመኪና መንገዶች በደረጃው ከፍ ያለ ይመስላል፡፡ [በሀገራችን አምረው የተሰሩ የመኪና መንገዶች በጥቂት ዓመታት ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ የመቦርቦር፣ የመፈረካከስ፣ ውሃ የማቆር ችግሮች ገጥሟቸው እንዲሁም ከመንገዱ ዳር እና ዳር የሚገኙ የብረት አጥሮች ተሰርቀው፣ ተገጭተው፣ ተጨረማምተው፣ ተነቃቅለው … አደጋ ሲያደርሱና የተለመደ የሬንጅ የመለጠፍ ሥራ ሲሰራላቸው በገሃድ የምናየው ሀቅ መሆኑን ማስታወስ ግን የግድ ይላል] ይሄኛው መንገድ ከጠቀስኳቸውና ካልጠቀስኳቸው ችግሮች ምን ያህለ ነጻ ነው? ለሚለው ትክክለኛ መስክርነት መስጠት ያለበት ለእውነት የቆመ የዘርፉ ባለሙያ ቢሆንም በኢህአዴግ ‹ልማት› ላይ የጥራት መተማመኛ ማግኘት እጅግ ከባድ መሆኑን ግን አምናለሁ፡፡ አስፋልቱ ለፍጥነት አመቺ መሆኑን ግን በቀላሉ መረዳት ይቻላል፡፡

በሶስት ሰዓታት ጉዞ ዝዋይ በመድረስ ምሳ ከበላን በኋላ ወደእስር ቤቱ የፈረስ ጋሪ መጠቀም ግዴታችን ነበር፡፡ አቧራማው አስቸጋሪ መንገድ፣ ከፊሉ ደቃቅ አሸዋ መልበስ ጀምሯል፡፡ የእስር ቤቱ የማስፋፊያ ግንባታ ሥራ፣ በፊት ውብሸትን ለመየጠቅ ስመጣ ከማውቀው ተፋጥኗል፡፡ አንዱ የሥርዓቱ “የልማት ውጤት” እስረኛ ማብዛት አይደለ ታዲያ?!
ከቀኑ 7፡30 ሰዓት ላይ የምንጠይቀውን እስረኛ በማስመዝገብ ተፈትሸን ገባን፡፡ ሁለት እስረኛ በአንዴ መጠየቅ ስለማንችል እኔ ተመስገን ጋር፣ አቤል ደግሞ ውብሸትን ለመጠየቅ ተስማምተን ነበር፡፡ አቤል ውብሸትን ከጠየቀ በኋላ እንደምንም ብሎ ተመስገንን ለመጠየቅ ጥረት እንደሚያደርግ ግን ቀድሞ ነገረኝ፡፡

ተመስገን እና ውብሸት የታሰሩበት ዞን ስለሚለያይ እኔ እና አቤል ሌላ የውስጥ ፍተሻ ካደረግን በኋላ መለያየታችን ግድ ነበር፡፡ የእስር ቤቱ ፖሊሶች የሚኖሩበትን ጉስቁልና ያጠቃቸው፣ መኖሪያ ቤቶችን አልፌ መጠየቂያው ጋር ደርሼ የታሳሪው ስም ያለባትንና በፖሊሶች የምትጻፈዋን ቁራጭ ወረቀት እስረኛን ለሚጠራው ፖሊስ ሰጠሁትና በአጣና እንጨት ርብራብ በተሰራው መጠየቂያው አግዳሚ ላይ ተቀመጥኩ፡፡ ከቅርብ ርቀት የፖሊሶች ማማ ይታያል፡፡ መሳሪያ የታጠቁ ፖሊሶች ማማው ላይና ከማማው ሥር በዛ ብለው ተቀምጠው ያወጋሉ፡፡ አብዛኞቹ ፖሊሶች ከላይ የለበሷት እና “Federal prison” የሚል የታተመባት አረንጓዴ ዩኒፎርምም በፀሃይ ብዛት ነጣ ወደማለት ደርሳለች፡፡ አንዱ ፖሊስ መጣና ከእኔ በትንሽ ሜትር ራቅ ብሎ ተቀመጠ፡፡ ‹‹አዳማጭ ነው›› አልኩ በልቤ፡፡ ወደፊት ለፊቴ ወደሚታየኝ የእስር ቤት ግቢ አማተርኩ፡፡ ለእይታ የሚጋብዝ አንዳች ነገር አጣሁ፡፡ የተበታተኑ ዛፎች፣ ቅርጽ አልባ ሳሮች፣ አስታዋሽ ያጡ አረሞች፣ ግድግዳ እና ጣራቸው በቆርቆሮ የተሰሩ የእስረኛ መኖሪያዎች፣ …ብቻ ጭርታ እና ድብታ የወረረው የግዞት መንደር ይመስላል፡፡

ከአንደኛው የእስረኛ ቆርቆሮ ቤት ጣሪያ ላይ ሁለት ተለቅ ተለቅ ያሉ ሙቀት ማቀዝቀዣዎች ይሽከረከራሉ፡፡ ወደፖሊሱ ዞሬ ‹‹ለሙቀት ነው?›› አልኩት ወደ ጣራው በመጠቀም፡፡ ‹‹አዎ፣ ወባ አደገኛ ነው›› አለኝ፡፡ ‹‹እስረኞች ሲታመሙ እንዴት ይሆናሉ?›› ስል ጥያቄ ሰነዘርኩ፡፡ ‹‹ያው እዚሁ ይታከማሉ›› አለኝ ድምጹን ቀሰስ አድርጎ፡፡ የእኔም ሆነ የእሱ ልብ፣ በማረሚያ ቤቱ (በእነሱ አጠራር) በቂ ህክምና እንደማይሰጥ ግን ያውቃል ብዬ አሰብኩ፡፡ ቀጭኑ ፖሊስ፣ ‹‹ለወባ ህመም ምግብ ወሳኝ ነው›› አለኝ አስከትሎ፡፡ ‹‹በቂ ምግብ የለም ማለት ነው?›› ስል ድጋሚ ጠየኩት፡፡ ‹‹በፊት በፊት አቀራረቡ ዝም ብሎ ነበር፤ ሙያ ባሌላቸው ሴቶች ነበር የሚሰራው፡፡ አሁን ግን ለውጥ አለ›› አለኝ፡፡ ‹‹ምን አይነት ለውጥ? ጥቂትም ቢሆን ታስሬ፣ ለእስረኞች የሚቀርበውን በጣም ደረጃውን ያልጠበቀ ምግብ አይቻለሁ›› አልኩት፡፡ ‹‹በፊት ጥቁር ጤፍ ነበር የሚቀርበው፤ አሁን የነጭ ጤፍ እንጀራ ነው የሚበሉት፤ እስረኞች ችግር የለባቸውም፤ ባለሙያ ሴቶችም ናቸው የተቀጠሩት …›› ‹‹(ውስጤ አላመነምና) ለእስረኛ የነጭ ጤፍ እንጀራ እያቀረባችሁ ነው?!›› …‹‹አዎ›› ብሎ ሊያብራራልኝ እያለ ከታች ከርቀት ‹‹አረንጓዴ ኮፊያ፣ ቲ-ሸርትና ስካርፍ ያደረገ ሰው አየሁ፡፡ ትኩረቴን ከፖሊሱ አዙሬ ቁልቁል ተመለከትኩ – ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ነበር፡፡ ተሜም፣ ረጋ ብሎ በራስ በመተማመን መንፈስ ወደመጠየቂያው ሥፍራ ቀረብ ብሎ ጠያቂውን ለማወቅ ጥረት አደረገ፡፡ ሳየው አንዳች የሀዘን ስሜት ውስጤ ገባ፡፡ ቆሜ ጠበኩት፡፡ ፈገግ እያለ መጣና ተጨባብጠን አራት አምስቴ ያህል ተቃቀፍን፡፡ ‹‹በዚህ በጸሐይ ለምን መጣህ?›› ሲል ጠየቀኝ፡፡ ከአቤል ጋር መምጣታችንን፣ እሱ ውብሸትን ሊጠይቀው መሄዱን ነገር ግን ከቂሊንጦ በኋላ እስከአሁን ዝዋይ ድረስ መጥቼ ባለመጠየቄ የጸጸት ስሜት ውስጤ እንዳለ ገለጽኩለት፡፡ ‹‹መንገዱ ረዥም ነው፣ ባትመጡም እረዳለሁ›› ካለ በኋላ፤ ‹‹ምን አዲስ ነገር አለ?›› በማለት ፊት ለፊት በእንጨት አጥር ተከልለን በመቀመጥ ጨዋታችንን ቀጠልን፡፡

‹‹አሁን ምን እየሰራችሁ ነው?››፣ ‹‹ክስህስ እንዴት ሆነ?››፣ ‹‹አዲስ ጋዜጣ ለማቋቋም ለምን ጥረት አታደርጉም?›› ከተመስገን በተከታታይ የተነሱ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ አጠር አጠር አድርጌ መለስኩለት፡፡ የጋዜጣ /የመጽሔት ህትመትን ድጋሚ መጀመር የግድ አስፈላጊ መሆኑን ግን ተመስገን አጽንኦት የሰጠበት ጉዳይ ነበር፡፡ …ስለተወሰኑ ጋዜጠኞችና የዞን 9 ጦማሪያን ከእስር መፈታት፣ ስለኦባማ የአዲስ አበባ ጎብኝት፣ በቂሊንጦ ዞን አንድ ከእነአብበከር አህመድ፣ ጦማሪ አቤል ዋበላና ዘላለም ክብርት ጋር ስለነበረው ቆይታ፣ እሱ ወደዝዋይ ከወረደ በኋላ እኔም በዚያ ዞን ገብቼ በነበረበት ጊዜ እነአቡበከር፣ አቤልና ዘላለም እሱን በተመለከተ ስለነገሩኝ ነገሮች ሳቅ እያልን አወጋን፡፡

ሰፊ ውይይት ያደረግነው በሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ላይ በቅርቡ ከ7 እስከ 22 ዓመት የሚደርስ ጽኑ እስራት ፍርድን በተመለከተ ነበር፡፡ ‹‹እኛ ከሙያ ጋር በተያያዘ ነው የታሰርነው፡፡ ታስረንም እንወጣለን፡፡ ከባዱ የሙስሊሞቹ እስር ነው፡፡ ኢህአዴግ እውነተኛ ሰላም ከፈለገ እነአቡበከርን በነጻ መፍታት አለበት፡፡ እኔ የእነሱ መከላከያ ምስክር ሆኜ ምስክርነቴን ሰጥቻለሁ፡፡ በወቅቱ ዘንግቼው ያልተናገርኩት አንድ ነገር ነበር፤ አሁን ሳስበው ትንሽ ይቆጨኛል – በተናገርኩ ብዬ፡፡ ያኔ (በምስክርነት ጊዜ)፣ ‹የኮሚቴዎቹ እንቅስቃሴ ሰላማዊ ነበር ወይስ አልነበረም?› የሚለው ጥያቄ በራሱ መነሳት አልነበረበትም፡፡ እንቅስቃሴያቸው፣ ሰላማዊ ባይሆን ኖሮ እንዴት ሶስት ዓመት ሙሉ በክስ ሂደት ይቀጥላል?! ሰላማዊ ስለሆኑ እኮ ነው፣ ባለፉት ሶስት ዓመታት ምንም ያልተፈጠረው፡፡ እስኪ በእነሱ አንድ የተሰበረ መስታወት አለ?! ቅንጣት የወደመ ንብረት አለ?! የማንንስ ሕይወት አጠፉ?! በእነሱ የተፈጠረ አንድም ነገር የለም፡፡ ጥያቄያቸው ኃይማኖታዊ እንጂ ፖለቲካዊ አይደለም፡፡ ፖለቲካዊ ቢሆን ኖሮ ትግሉ አቅጣጫውን ይቀይር ነበር፡፡ ‹የመጅሊስ አመራሮችን ካለመንግሥት ጣልቃ ገብነት እንምረጥ!› ነው አንዱ ሰላማዊ ጥያቄያቸው፡፡ ያው ምስክር ስትሆን ከዚህም ከዚያ ጥያቄ ሲነሳ ስለምትዘናጋ መመስከር ያሰብከውን ነው ቅድሚያ የምትሰጠው እንጂ አሁን የምልህን ያኔ ብገልጸው በጣም ደስ ይለኝ ነበር …›› በማለት በኢትዮጵያ ውስጥ ከታሪክ አኳያ፣ በሁለቱ ትልልቅ ሃይማኖት ተከታዮች መካከል ስለነበረው ግንኙነት በዝርዝር የራሱን ምልከታ እና ሀሳብ ደጋግሞ አወጋኝ፡፡ ኃይማኖታዊ መቻቻል ነበር ወይስ አልነበረም? የሁለቱም እምነት ተከታዮች ጉርብትና ነበራቸው ወይስ አልነበረባቸውም በሚሉት አንኳር ጉዳዮችም የራሱን አቋም አንጸባረቀልኝ፡፡
ኡስታዝ አቡበከር አሕመድን አስመልክቶም አንድ ጥሩ ምሳሌም አንስቶልኝ ነበር ተመስገን፡፡

‹‹አሁን ባለሁበት ዞን፣ በአንድ የወንጀል ክስ ግብረ-አበር ተብለው አምስት ዓመት የተፈረደባቸው አንድ ቄስ አሉ፡፡ እኚህ ቄስ ለጠበቃ የሚከፍሉት አጥተው የጠበቃ ክፍያ የፈጸመላቸው አቡበከር እንደሆነ ነግረውኛል››
እኔም ፣ በህዳር ወር ቂሊንጦ ዞን አንድ በነበርኩበት ጊዜ ከዚህ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ነገር፣ ስለአቡበከር ሰምቼ ነበር፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡- አንዱ እነአቡበከር ይገኙ በነበረበት ዞን 1 8ኛ ቤት ውስጥ የቀጠሮ እስረኛ ነበር፡፡ ዋስትና ይጠየቅና በዚህ ክፍል ውስጥ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው የታሰሩ አንድ የናጠጡ ሀብታም (ልጃቸው 22 አካባቢ እጅግ ዘመናዊ ሆቴል አለው) ጋር ጠጋ ብሎ ለዋስትና የሚሆን ብር ተጨንቆ በአክብሮት ይጠይቃቸዋል፡፡ እሳቸውም ‹‹እኔም እንደአንተው እስረኛ እኮ ነኝ!›› በማለት ይመልሱለታል፤፡፡ ልጁም ያዝናል፡፡ ይህ ጉዳይ አቡበከር ጆሮ ይገባና ለልጁ የሚስፈልገውን የዋስትና ብር ከፍሎ ልጁን ከእስር እንዲወጣ አድርጎታል፡፡ እንግዲህ፣ ከሁለቱ እውነተኛ ምሳሌዎች በመነሳት፣ አቡበከር ለወገኖቹ ሃይማኖትን መሰረት ሳያደርግ፣ በሰብዓዊነት ደግ መሆኑን እንማራለን፡፡

ከተመስገን ጋር በነበረን ሰፋ ባለ የጨዋታ ጊዜ፣ ከጎኔ የነበረው ፖሊስ በተመስጦ ቢያዳምጥም፣ አንዴም አላቋረጠንም ነበር፡፡ …ስለ 100% ቱ የዘንድሮ ምርጫ ፍጻሜ፣ በሰሞኑ በአፋር ክልል ስለደረሰው የድርቅ አደጋ፣ በአይ ኤስ አሸባሪ ቡድን ስለተቀሉና ስለተገደሉት ኢትዮጵያኖች፣ ድርጊቱን በማውገዝ በመስቀል አደባባይ በተጠራው ሰልፍ ላይ ስለተፈጠረው ረብሻ፣ ጉዳትና እስር ተመስገን የራሱን አተያይ በስሜት ተውጦ የግሉን ሀሳብ አብራራልኝ፡፡ በተጨማሪም፣ አይ ኤስ ያንን ድርጊት፣ ያንን ጊዜ መርጦ አደረገ ያለበትን የራሱን የተለየ (ከማንም ያላደመጥኩትን፣ ተጽፎም ያላነበብኩትን) ሀሳብ አጋራኝ፡፡ የተለየ ሃሳብ በመሆኑም ‹‹አሃ!›› ብያለሁ፡፡

ከተመስገን በጣም የገረመኝ፣ የማስታወስ ችሎታው ነበር፡፡ በጥቅምት ወር፣ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ‹‹ጥፋተኛ›› በተባለበት ማግስት ጥዋት አምስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ልጠይወቅ ሄጄ በማያመች ሁኔታ ውስጥ ሆነን አብዮትን አስመልክቶ የተለዋወጥናቸውን ሃሳቦችን፣ እንዲሁም ከአቤል ጋር ቂሊንጦ ስንጠይቀው ያነሳናቸውን ሀሳቦች ድጋሚ በማስታወስ በዚህ ቀን ለተነሱት ርዕሰ ጉዳዮች የውይይት ማጠናከሪያ ሀሳብ ሲያደርጋቸው አስተውያለሁ፡፡

ለተመስገን አሁን ስለሚገኝበት ዞን ሁኔታ ጥያቄ አቀረብኩለት፡፡ ቀደም ሲል ከእነውብሸት ጋር አብሮ እንደነበረ ጠቅሶ፣ ‹‹የኢትዮጵያ ገመና›› በሚል ርዕስ በእስር ቤት ውስጥ ስላወቀው ነገር ሁለት ተከታታይ ጽሑፎችን ካወጣ በኋላ ወደዚህ ዞን መዘዋወሩን ይገልጻል፡፡ አሁን ባለበት ክፍል 80 የሚሆኑ እስረኞች አብረውት አሉ፡፡ ብዙዎቹ ከደቡብ ክልል የመጡ ናቸው፡፡ ከእሱ ጋር አንድም የፖለቲካ እስረኛም ሆነ ጋዜጠኛ አብሮት የለም፡፡ [አቶ በቀለ ገርባ ከወራቶች በፊት የ3 ዓመት ከ7 ወር የእስር ጊዜያቸውን አጠናቅቀው ከዝዋይ እስር ቤት በተፈቱ ማግስት ተመስገን ከባድ ወደሆነው ወደዚህ ዞን መሸጋገሩን ነግረውኝ ነበር] አሁን ባለበት ዞንም ከእሱ ጋር እስረኞች እንዳያወሩ እና እንዲያገልሉት በዘዴ ተደርጓል፡፡ ከእሱ ጋር በቅርበት ሆነው የሚያወሩ ካሉ፣ እንደትልቅ ተስፋ በሚጠብቁት አመክሯቸው ላይ እንደመፍረድ ይቆጠራል እንደተመስገን አባባል፡፡ ‹‹በዚህ ጉዳይ ማናቸውም ላይ አልፈርድም፤ ከእኔ ጋር አውርተው የአመክሮ ጊዜያቸውን እንዲያጡ አልሻም፡፡ ግን እንዲህ ያደረጉት ሌሎች የፖለቲካ እስረኞች ቢሆኑ ኖሮ ይሰማኝ ነበር፡፡›› ሲል ያለበትን ከባድ ሁኔታ ያስረዳል፡፡

‹‹ማንበብ፣ ማጸፍስ ትችላለህ?›› ሌላኛው ጥያቄዬ ነበር፡፡ ‹‹መጽሐፍ አይገባም ተልክሏል፤ ያነበብኳቸው ጥቂት ልብወለድ መጽሐፍቶች አሉ፡፡ መጻፍ ትንሽ ጀምሬ በእስረኞች በኩል ተጠቁሞ የጻፍኩት ተወሰደ፡፡ ሁለት ሶስቴ ለመጻፍ ሞክሬ ነበር፡፡ ግን ተመሳሳይ እርምጃ በመወሰዱ ተውኩት፡፡›› ይላል ተመስገን፡፡ ‹‹ቀኑን እንዴት ነው የምታልፈው?›› የሚለው የመጨረሻ ጥያቄዬ ነበር፡፡ ‹‹ሁለት የማውቃቸው የአዲስ አበባ ልጆች አሉ፤ ጫናውን ችለው ያናግሩኛል፡፡ ከእነሱ ጋር ቼዝ እጫወታለሁ፡፡ የእግር ኳስ ፕሮግራም የሚተላለፍባቸው ቻናሎች ቢኖሩም መገለሉን አስበውና ደስ ስለማይለኝ ወደክፍሌ እገባለሁ›› የሚለው የተመስገን መልስ ነበር፡፡

ተመስገን አቤልን ከርቀት አይቶት ‹‹ያ አቤል ነው አይደለ?›› አለኝ፡፡ ዞሬ አየሁት፣ አቤል ውብሸትን ጠይቆት ከርቀት ወደመውጪያው በር እየሄደ ነበር፡፡ ‹‹ግን እንዴት አስገቧችሁ?፤ ይመልሱ ነበር እኮ›› አለኝ፡፡ አቤልም ተመስገንን ተመስገንም አቤልን ማግኘት ፈልገው ነበር፡፡ ብዙም ሳይቆይ አቤል አንዱን ፖሊስ እንደምንም አናግሮ ተመስገንን ሊጠይቅ መጣ፡፡ ተቃቅፈው ተሳሳሙ፡፡ የሶስትዮሽ ጨዋታችንን ለግማሽ ሰዓት ያህል አደራነው፡፡ ተመስገን ከታሰረ በኋላ የግራ ጆሮው እንደማይሰማለት እና ወገቡም ሕክምና በማጣቱ አሁንም ድረስ እንደሚያመው አልሸሸገንም – ‹‹እዚህ ያለው መድኃኒት ፓናዶል ብቻ ነው›› በማለት፡፡ አያይዞም ‹‹ሰው መጥቶ ሲጠይቅህ ደስ ይላል፤ ጥሩ እንቅልፍ ትተኛለህ፤ግን የመንገዱን ርቀት ሳስበው ሰው ባይመጣ እላለሁ›› አለን በድጋሚ፡፡

የእስረኛ መጠየቂያ ጊዜ መጠናቀቁን ፖሊሶች ነገሩንና ተቃቅፎ መለያት ግድ ሆነ፡፡ ‹‹አይዞህ የምትባል አይደለህምና ሰላም ሁን›› አልኩት፡፡ ‹‹ምን መልዕክት አለህ?›› ስል የመጨረሻ ጥያቄዬን ሰነዘርኩለት፡፡ ተመስገንም ‹‹ታገሉ!›› ሲል መለሰና በመጣበት መንገድ ቻው ብሎን እርምጃውን ቀጠለ፡፡ ሲሄድ አራት እና አምስት ጊዜ ያህል ዞረን አየነው፡፡ ስለገኘነው ደስ ቢለንም በሳሮች መካከል ባለው መንገድ ወደታሰረበት ክፍል ሲያመራ ማየት ዳግመኛ የመረበሽ እና የማዘን ስሜት በውስጤ ፈጥሮብኝ ነበር፡፡ ስሜቱ በጣም የሚገባው በቦታው ላይ ሲገኙ ነው!
ተመስገን፣ ያመነበትን ሀሳብ በድፍረት ስለጻፈ ነበር በኢ-ፍትሃዊነት ሶስት ዓመት እስር የተፈረደበት፡፡ ሰው መታሰሩ ሳያንስ፤ ከቤተሰቡ፣ ከወዳጁ፣ ከዘመዱ፣ ከጓዳኞቹ እርቆ እንዲታሰር ማድረግ ሌላ ቅጣት ነው! ሰው መታሰሩ ሳያንስ፣ ህክምና መከልከሉ፣ በሌሎች እስረኞች እንዲገለል መደረጉ፣ መጽሐፍ ማንበብ እና የግል ማስታወሻዎቹን እንዳይጽፍ መከልከሉ ይሄም ሌላ ቅጣት ነው! ሰው ግን በስንቱ ይቀጣል?! እንዲህም ሆኖ፣ ትናንት የምናውቀው ጋዜጠኛ ተመስገን፣ አሁንም ድረስ ያ ያመነበትን የመናገር ድፍረቱ፣ መንፈሳዊ ብርታትና ጥንካሬው አብሮት አለ!!! አካል ቢታሰር ህሊና መቼም አይታሰር!!!

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!

Wednesday 5 August 2015

የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለ3ኛ ጊዜ አቶ አንዳርጋቸውን አላቀረበም

‹‹ቤተሰቦቼ አሸባሪ ተብለው ቤት የሚያከራያቸው አጥተዋል፤ ልጆቼ በረንዳ ላይ ወድቀዋል፤ ቤተሰባችን ተበትኗል››
ም/ኢንስፔክተር ሙልዬ ማናዬ ረታ (7ኛ ተከሳሽ)

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
በዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ እስከ 5ኛ ለተከሰሱት አቶ አሸናፊ አካሉ (2ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ደናሁን ቤዛ (3ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን (4ኛ ተከሳሽ) እና አቶ አንሙት የኔዋስ (5ኛ ተከሳሽ) ዋስ እንዲሆኑ ለዛሬ ሀምሌ 29/2007 ዓ.ም ፍርድ ቤት እንዲያቀርብ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ የደረሰው የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ሳያቀርብ ቀርቷል፡፡

ተከሳሾቹ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርቡላቸው የጠየቁት የፌደራል አቃቤ ህግ ‹‹ከአንዳርጋቸው ፅጌና ፋሲል የኔዓለም እንዲሁም ከሌሎቹ የአሸባሪው ድርጅት አመራሮች ጋር በአካልና በሌሎች የመገናኛ ዘዴዎች በመገናኘት ስለ ሽብር ተግባሩ አፈፃፀም በመግባባት፣ ኤርትራ ወደሚገኘው የግንቦት ሰባት ካምፕ ሄደው ስልጠና በመውሰድ፣ ተልዕኮ ተቀብሎ ወደ ሀገር ውስት በመመለስ፣ ....›› የሚል ክስ ስለመሰረተባቸው ነው፡፡

የልደታ ፍርድ ቤት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ በዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ እስከ 5ኛ ለሚገኙት ተከሳሾች ሀምሌ 13/2007 ዓ.ም ልደታ ፍርድ ቤት ቀርበው ምስክርነት እንዲሰጡ ወስኖ የነበር ቢሆንም ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚላከው ማዘዢያ እንደዘገየ በመግለጽ ለሀምሌ 15/2007 ዓ.ም እንዲቀርቡ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወቃል፡፡ ሆኖም አቶ አንዳርጋቸው ሀምሌ 15/2007 ዓ.ም ያልቀረቡ ሲሆን ማረሚያ ቤቱ ትዕዛዙ ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት መጻፍ ሲገባም ለአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት ተብሎ ስተለጻፈ ማቅረብ እንዳልቻለ ገልጾ ነበር፡፡ ፍርድ ቤቱም ማዘዢያው ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት ተብሎ እንዲፃፍ አዝዞ ለሶስተኛ ጊዜ ማረሚያ ቤቱ ለሀምሌ 29/2007 ዓ.ም አቶ አንዳርጋቸውን እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ ይሁንና በዛሬው ዕለትም የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ሳያቀርብ ቀርቷል፡፡ ፍርድ ቤቱ አቶ አንዳርጋቸው ምስክር እንዲሆኑ ከወሰነ ጊዜ ጀምሮ ይቀርባሉ ተብለው ሳይቀርቡ ሲቀሩ የዛሬው ለሶስተኛ ጊዜ ነው፡፡

በዛሬው ዕለት የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ለምን እንዳላቀረበ እንዲያብራራ፣ እንዲሁም በዛው ቀን ለምስክርነት እንዲያቀርብ ሲል ለጥቅምት 12/2008 ዓ.ም ለአራተኛ ጊዜ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ተከሳሾቹ አጭር ቀጠሮ ተሰጥቶ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት አቶ አንዳርጋቸውን ለምን እንዳላቀረበ ማብራሪያ እንዲሰጥ ቢጠይቁም ፍርድ ቤቱ በሌሎች መዝገቦች የሚሰሙ ምስክሮች ስላሉና ከነሀሴ 15/2007 ዓ.ም በኋላ ፍርድ ቤት ስለሚዘጋ በሚል አቤቱታቸውን አልተቀበለውም፡፡
በሌላ በኩል በማረሚያ ቤትና በፍርድ ቤቱ ችግር አቶ አንዳርጋቸውን ለምስክርነት ማቅረብ ባለመቻሉ እየተጉላሉ መሆናቸውን ተከሳሾቹ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡ 7ኛ ተከሳሽ ም/ኢንስፔክተር ሙልዬ ማናዬ ‹‹የአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት በመባሉ በሚል ተልካሻ ምክንያት ለምን እንጉላላለን? እኛ ፍትህ ፈላጊ ነን፡፡ ቃሊቲና ቂሊንጦ በአንድ ደቂቃ የስልክ ግንኙነት መገናኘት እየቻሉ በቀጠሮ እየተጉላላን ነው›› ብለዋል፡፡

ተከሳሹ አክለውም ‹‹እኔ የመከላከያ ምስክሬን ያቀረብኩት የዛሬ አመት ነው፡፡ ለእኔ ብለው ቤተሰቦቼ በሬያቸውን ሸጠዋል፡፡ ግን አሁንም ድረስ እየተጉላላሁ ነው፡፡ ቤተሰቦቼ አሸባሪዎች ናቸው ተብለው ቤት የሚያከራያቸው አጥተዋል፡፡ ልጆቼ በረንዳ ላይ ወድቀዋል፡፡ ቤተሰባችን ተፈትቷል፡፡ ምስክሩን ማቅረብ ካልቻሉ ለምን ክሱን ውድቅ አታደርጉትም?›› ሲሉ የፍርድ ሂደቱ በመጓተቱ እየደረሰባቸው የሚገኘውን በደል ገልጸዋል፡፡

የፌደራል አቃቤ ህግ ‹‹የአማራ ክልል ወጣቶች ፕሬዝደንት ሆኖ ባለበት በሐምሌ ወር 2004 ዓ.ም በኬንያ አድርጎ ከሀገር ከወጣ በኋላ የአሸባሪውን የግንቦት 7 ልዩ ኃይል (Popular Force) ታጥቆ እየተንቀሳቀሰ የሚገኝ›› በሚል በሌለበት ክስ የመሰረተበት የዠመነ ካሴ ክስ መዝገብ 10 ተከሳሾቹ የተከሰሱ ሲሆን 10ኛ ተከሳሽ ወ/ሮ ሙሉ ሲሳይ መቆያ የአቃቤ ህግ ምስክር ሆና ግንቦት 19/2006 ዓ.ም በነፃ ተለቃለች፡፡

Monday 3 August 2015

በእነ አቡበክር አህመድ የክስ መዝገብ የተጠቀሱ 18 ተከሳሾች ከ22 እስ ከ 7 አመት ፈረደባቸው


22 አመት የተቀጡት ፍርድ ቤቱ በሽብር ወንጀሉ ከፍተኛ ሚና ነበራቸው ያላቸው አቡበክር አህመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ ያሲን ኑሩ እና ከሚል ሸምሱ ናቸው ። ችሎቱ በመዝገቡ የተጠቀሱ 5ኛ፣ 7ኛ፣ 8ኛ፣ 11ኛ እና 15ኛ ተከሳሾችን፥ በድሩ ሁሴን፣ ሳቢር ይርጉ፣ መሃመድ አባተ፣ አቡበክር አለሙ እና ሙኒር ሁሴንን እያንዳንዳቸውን በ18 አመት ጽኑ እስራት ቀጥቷቸዋል ።

ሼህ መከተ ሙሄ፣ አህመድ ሙስጠፋ፣ ሼህ ሰኢድ አሊ፣ ሙባረክ አደም እና ካሊድ ኢብራሂም የ15 አመት ጽኑ እስራት ተወስኖባቸዋል ። እንዲሁም ሙራድ ሽኩር፣ ኑሩ ቱርኪ፣ ሼህ ባህሩ ዑመር እና የሱፍ ጌታቸውን በ7 አመት ጽኑ እስራት ቀጥቷቸዋል ። ተከሳሾችም ይሁን ከሳሽ አቃቤ ህግ የቅጣት አስተያየት እንዲያቀርቡ የ10 ቀን ጊዜ በችሎቱ ተሰጥቷቸው የነበረ ሲሆን ፥ አቃቤ ህግ ቀድሞ ማቅረቡን ችሎቱ አትቷል ።

ተከሳሾች የአቃቤ ህግን የቅጣት አስተያየት ካላየን አናቀርብም ማለታቸውን ተከትሎ ችሎቱ የአቃቤ ህግ የቅጣት አስተያየት እንዲደርሳቸው ትዕዛዝ አስተላልፎ ነበር ።

ይሁን እንጂ ከተሰጣቸው የመጀመሪያው 10 ቀን ሌላ ተጨማሪ ቀን ቢሰጣቸውም የቅጣት ማቅለያ ሊያቀርቡ አልቻሉም ።
ፍርድ ቤቱ ቅጣቱን ያስተላለፈው አቃቤ ህግ ተከሳሾች ወንጀሉን የፈጸሙት በስምምነትና በአንድነት ነው የሚለውን የቅጣት ማክበጃ ተቀብሎ ነው ።

ችሎቱ ከእስራት ቅጣት በተጨማሪ ተከሳሾች ይህ ውሳኔ ከፀናበት እለት ጀምሮ ለአምስት አመታት እንዳይመርጡ ፣ እናዳይመረጡ ፣ በየትኛውም ቦታ ዋስም ምስክርም እንዳይሆኑ በአጠቃላይ ከማህበራዊ መብታቸው አግዷል ።

የፍርዱን ሂደት ለመከታተል፣ ለመሪዎቻቸው ያላቸውን አክብሮት ለማሳየት እና አጋርነታቸውን ለመግለጽ ከወትሮው በተለየ መልኩ የሙስሊሙ ማህበረሰብ አባላት በርከት ብለው በፍርድ ቤቱ ተገኝተዋል።

ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች “ከወያኔ የካንጋሮ ፍርድ ቤት ከዚህ የተለየ ነገር አልጠበቅንም ነበር” ብለዋል።
“ከዝንብ ማር አንጠብቅም” እያሉ ያሉት ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ወደፊትም በኢትዮጵያ የሐይማኖት ነጻነት እና እውነተኛ ዲሞክራሲ እስኪመጣ ድረስ ትግላችንን አናቆምም ብለዋል።