Wednesday 30 September 2015

ኢትዮጵያዊ ማንነት እንዴት ያለ ነው? ኢትዮጵያዊ አንድነትስ ምን ይመስላል? (የግል እይታ – ዮናታን ረጋሳ)


እውን ኢትዮጵያዊነት ወይም የኢትዮጵያ አንድነት ሲባል በሁላችንም አእምሮ ውስጥ አንድ አይነት ምስል ይከሰታል? አንድ አይነት ትርጓሜስ ይኖረዋል?

አንዳንዴ ሳስበው በእያንዳንዳችን አእምሮ ውስጥ ያለውን የኢትዮጵያዊነት እይታ ወደ ውጪ አውጥተን ብናስተያየው አንዱ ከአንዱ እጅግ የተለየ እንደሚሆን አልጠራጠርም፡፡ አንድነት/ ኢትዮጵያዊነት የሚለው እሳቤ በመርህ ደረጃ ሁሉም የሚቀበለው ሸጋ ሀሳብ ቢሆንም በአረዳዳችን ላይ ግን እጅግ እንደምንለያይ ይሰማኛል፡፡ ይህን ፅሁፍ ማዘጋጀቴም በዚሁ ጉዳይ ዙሪያ የተለያየ ስሜት እንዲፈጠር ምክንያት የሚሆኑ ነገሮችን አውቆ መመርመር እና መረዳት ምናልባትም የተቀራረበ እይታ ለመፍጠር ይረዳል ብዬ ስለማስብ ነው፡፡ በቀናነት ታነቡልኝ ዘንድ እጠይቃለሁ!

በኔእምነት በኢትዮጵያ ግዛት ስር ያለው ሁሉ ኢትዮጵያዊ ነው ቢባልም ቅሉ ከቦታ ቦታ ያለው የኢትዮጵያዊነት ስሜት ግን የተለያየ ነው፡፡ ግለኝነት እና አለማቀፋዊነት ተፅዕኖ ስር ያለ ማንነት፤ ከተለያየ የህብረተሰብ ክፍል በመወለድ(ቅይጥ በመሆን) የሚፈጠር ማንነት፤ በፖለቲካ የተቃኘ ታሪክን (politicized narrative of history) መሰረት ያደረገ ማንነት፤ ያለፉ ነገስታት እና ገዢዎች የእርስ በእርስ ጦርነት ባስከተለው ‘የእኔ እበልጥ እኔ እበልጥ’ ስነልቦና የተፈጠረ ማንነት፤ በነገስታቱ እና በፈላጭ ቆራጮች አምሳል ተገንብቶ ተከታይ ያፈራ ማንነት . . . እና የመሳሰሉት ሁኔታዎች የሚፈጥሯቸው ማንነቶች ተደባልቀው በውጥረት ውስጥ የተገነባ አንድነት መገለጫችን ይመስለኛል፡፡

በመሰረቱም ኢትዮጵያዊነትም ሆነ የኢትዮጵያ አንድነት ወጥነት ያለው አይደለም፡፡ በዘመነ መሳፍንት ተበታትኖ የነበረው ሀገሪቱ ክፍል በነ አፄ ሱስኒዮስ ከነበረው ሰፊ የግዛት ክልል በፍፁም የተለየ ነው፡፡ አፄ ቴዎድቶስ ያቀኑት ሀገር አፄ ምኒልክ ካቀኑት ሀገር የተለየ ነው፡፡ አፄ ምኒልክ ይገዙት የነበረው ሀገር በቀኃሥ እና በኮምኒስት ኢትዮጵያ መልኩን እየቀያየር አልፎ አሁን ላይ አድርሶናል፡፡ የማንነት ትርክቱም ሆነ የአንድነት ይዘቱ በነዚሁ ዘመናቶች እንደገዢዎቹ የተለያየ ነው፡፡

ይህ ልዩነት በየዘመኑ ከተነሱ ነገስታት እና ፈላጭ ቆራጮች ፍላጎትና ህልም ጋር ተሳስሮ አሁን ካለንበት ዘመን ያደረሰን ሲሆን፤ ህዝቡ ግን ከገዢዎቹ ፍላጎት ውጪ የራሱን እድል በራሱ የወሰነበት አንድነቱንም ሆነ ማነቱን በራሱ የማህበረሰብ ስብጥር አምሳል የፈጠረበት ጊዜ የለም፡፡ (ይህ ሲባል ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ በርካታ ማህበረሰቦች የእርስ በእርስ ትስስር እና ዝምድና አልመሰረቱም ለማለት ሳይሆን – በዘመናት ውስጥ በነበረው የአንዱ አካባቢ ገዢ ሌላኛውን በጉልበት አስገብሮ ለመግዛት በተደረጉ ጦርነቶች ከቦታ ቦታ የተለያየ ስነልቦና የተላበሱ ማህበረሰቦች እንደሚኖሩ ማድረጉ የሚካድ አለመሆኑን ለማመላከት ነው፡፡)
ለዚህም ነው የኢትዮጵያ አንድነት ተጀምሮ ያልተጠናቀቀ፤ ኢትዮጵያዊነት ሲባልም ወጥነት የሌለው ነው የሚል የመከራከሪያ ሃሳብ ለማንሳት የምወደው፡፡ በታሪክ አንዱ አንደኛውን ማህበረሰብ በጉልበት እያስገበረ አሁን ላይ ደረስን እንጂ – በየትኛውም የታሪክ አጋጣሚ በህዝቦች መተማመን እና መፈቃቀድ የተገነባ አንድነትም ይሁን ወጥ ኢትዮጵያዊ ማንነት ዛሬም ቢሆን የለንም፡፡ ኢህአዴግም ሆነ ፋሺስት ኢጣልያ የልዩነታችን ፈጣሪዎች ሳይሆኑ በዘመናት ውስጥ በተለያየ ትርክት የነበረ ልዩነታችንን ተጠቅመው ‘የከፋፍለህ ግዛ’ አገዛዝን ለማስፈን መሞከራቸውን መገንዘብ – በነሱ እያሳበቡ ልዩነትን በመሸፋፈን ለበለጠ ችግር ከመጋለጥ ያድናል፡፡

ከላይ ያሰፈርኩትን ሀቲት መሰረት አድርገን የከተሜውን (በተለይም የትልልቅ ከተሞች) የማህበረሰብ ክፍል የሚኖረውን ስነልቦና እንፈትሽ እና ወደ ቅድመ ነገራችን እንመለሳለን፡፡ (ይህን የመፈተሸ አስፈላጊነት ከተሜው በፖለቲካው ላይ የሚኖረውን ጉልህ ተፅዕኖ ታሳቢ በማድረግ ነው፡፡)
{{ከተሞች የነገስታት እና የፈላጭ ቆራጮች መቀመጫ የነበሩ ከመሆናቸው አንፃር (በአንዳንድ ስፍራ መስራቾቹም እነሱው ናቸው) የከተማው የማንነት እና ሀገራዊ አንድነት መንፈስ የነዚህኑ የገዢዎች እምነት የሚያንፀባርቅ ይሆናል፡፡ አንድነት የሚለውንም ሆነ ኢትዮጵያዊነት የሚለውን እሳቤ እንደ ገዢዎች እምነት፣ ፍላጎት እና ህልም የሚገነባ ነው፡፡ ወደነዚህ ከተሞች ከተለያየ ማህበረሰብ ክፍል ፈልሰው የሚመጡ ሰዎችም ከተሞቹ ውጠው የሚያጠምቋቸው ማንነት በነገስታቱ መልካም ፈቃድ የተገነባውን ማንነት ይሆናል፡፡ ወደ ከተማው የሚዋሃዱ ሰዎችም ይህንኑ የከተሜ ስነልቡና መላበስ እና እንደኖርም የተዘረጋውን ማንነት ተቀብለው መኖር ይጠበቅባቸዋል (ይመቻቸውም አይመቻቸውም)፡፡ እዚህ ላይ ልብ እንዲባል የሚያስፈልገው ነጥብ ታዲያ ነገስታቱም ሆነ ፈላጭ ቆራጮቹ ፍላጎታቸውም፣ እምነታቸውም ሆነ ማንነታቸው ከተፈጠሩበት ማህበረሰብ የሚመነጭ መሆኑና በሚገዙት ሀገር የሚያሰፍኑት ስርዓትም በዚሁ መልክ የሚቃኝ መሆኑ ነው፡፡}}

እንግዲህ ይህን ይዘን ስለ ታሪካዊ ዳራው እና የት እንዳደረሰን ጠቅለል ያለ ዳሰሳ እናድርግ –
ከላይ እንዳነሳሁት ‘ስዩመ እግዚአብሔር’ ገዢዎች በታሪክ አጋጣሚ የጀመሩት ‘ኢትዮጵያ’ የሚለውን ግዛት የማስፋፋት፤ በውስጡ ያቀፈውንም ማህበረሰብ የማዋሃድ (with their mighty)፤ በዚሁ ግዛትም ኢትዮጵያዊ የተሰኘ ማንነት የመገንባት ውጥናቸው ሳይቋጭ የዓለም ሁኔታ በፍጥነት መቀያየር ጀመረ፡፡ የዲሞክራሲ ጥያቄ በዓለም ጭቁን ህዝቦች ዘንድ እንደ ሰደድ እሳት ተዛመተ፡፡ በሀገራችን ኢትዮጵያም የዘመኑ የፖለቲካ አካሄድ በመቀየሩ ያስገበሩትም ሆነ የገበሩት ማህበረሰቦች ጨርሰው ሳይዋሃዱ የተነሳው የዲሞክራሲ ጥያቄ ሁሉም የማህበረሰብ ክፍል ስለህልውናውም ጭምር እንዲታገል የሚገፋፋ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ተከፈተ፡፡ የኢትዮጵያዊ ማንነትም ሆነ አንድነት አንዱ አንደኛውን እያስገበረ የመሆኑ ትርክት አክትሞ ሁሉም የማህበረሰብ ክፍል በእኩልነት እና በመተማመን ላይ ተመስርቶ በግዛቲቱ ውስጥ ውህደቱን የማካሄድ ጉዳይ 19ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ክስተት ሆነ፡፡ (ሜጫና ቱለማ፤ ቀዳማይ ወያኔ እንዲሁ ሌሎች ንቅናቄዎችም በዚሁ ማእቀፍ መታየት የሚችሉ እንደሆኑ ይሰማኛል)

በዚህ ታሪካዊ ኩነት የተፈጠሩ መልካም አጋጣሚዎች እና ንቅናቄዎች ግን በኣዳዲስ ጉልበተኞች እና ኋላቀር የስልጣን ጥመኞች ተጠለፉ፡፡ ግልፅ የነበረውን የሀገሪቷን የጦርነት ታሪክ አንዱ አንዱን በማስገበር ግዛት የማስፋፋት እና ማንነት የመገንባት የታሪክ ኩነቶችን የሚያዛቡ አዳዲስ የታሪክ ድርሳናት በብዛት ተከተቡ፡፡ የእነዚህ ድርሳናት ትርክትም በአመዛኙ የጉልበተኞቹን የስልጣን ፍላጎትና የፖለቲካ ዓላማ ለማሳካት የተፃፉ በመሆናቸው ብዙኃኑን ሰው የጠራ ምልከታ እንዳይኖረው አድርገዋል፡፡ አንዳንዶቹ የታሪክ ኩነቶችን የበቀል መሳሪያ ሊያደርጓቸው አዛብተው መርዝ እየረጩ ሲፅፏቸው፤ አንዳንዶች ደግሞ የተለያየ የታሪክ ኩነቶችን የተወሰነ የህብረተሰብ ክፍል ገድሎች ብቻ አድርገው ማቅረባቸው – በእኩልነት እና በመተማመን ሀገር ለመገንባት የተነሳሳውን ቀና መንፈስ እንዲጠለፍና ልዩነታችን የጠላትነት ስሜት መንሰራፊያ እንዲሆን በር ከፈተ፡፡

ሁሉም የየራሱን ፖለቲካዊ ትርክት እያበጃጀ ከሌላው ጋር ሊያግባቡት የሚችሉትን ድልድዮች በማፍረስ ተጠመደ፡፡ ስለማንነት በሚደረጉ ክርክሮችም ላይ አንዱ ትግሬ ነኝ ቢል ‘ዘረኛ’፤ ሌላው ኦሮሞ ነኝ ሲል ‘ጠባብ’፤ አማራ ነኝ የሚለውንም ደግሞ ‘አማራ በዚህ ደረጃ አይወርድም’ በሚሉ ሽምቀቃዎች እና ፍረጃዎች ቀናው መንፈስ በክፉ መንፈስ ተበከለ፡፡ ኢትዮጵያዊነቴን ብቻ ነው የማውቀው የሚልም ነፍጠኛ የሚል ማእረግ ተለጠፈለት፡፡ ኢትዮጵያዊነትም ለአንደኛው ወገን የመጨቆኛ መሳሪያ ሲሆን ለአንደኛው ወገን ደግሞ ሰው የመሆንና የሀገር ወዳድነት ደረጃን አጎናፀፈ፡፡ መጨቆኛ አይደለም የሚለው የጨቋኝ ጠበቃ ተደርጎ ሲሳል፤ በኢትዮጵያዊነት ላይ ነቀፋና ሂስ የሚሰነዝር ደግሞ ‘ውግዝ ከመ አርዮስ’ እየተባለ ተወገዘ፡፡ አፎች ተከፈቱ – አንደበቶች ተለጎሙ – ችግራችን ስር ሰደደ፡፡ እንግዲህ በሁለት ስለት መወጋት ለማንም አልበጀምና ሁሉም ወደመረጠው እና ወደወደደው ጎራ ገብቶ በጥርጣሬ መተያየት የወቅቱ እጣ ፈንታችን ሆነ፡፡

እኔ በፍቅር የነደድኩላት፤ ጠንካራ አንድነቷን የማልምላት ኢትዮጵያ እንግዲህ ይህን ትመስላለች፡፡ አንገቷን ተቀንጥሳም ትምህርት መውሰድ አቅቷት፤ ልሂቃኖቿም ጎራ ለይተው እንደተፋጠጡ፤ ከተሜውም በግላዊነት ግዴለሽ ስሜት ሲሰምርለት ወደ ሌላው የዓለም ክፍል እየሄደ ራሱን የአዲስ ማንነት ባለቤት ሲያደርግ – የተቀረው ደግሞ ከላይ በጠቀስኩት መልኩ በገዢዎች አምሳል የተፈጠረ ማንነት ላይ በፍቅር ተጣብቆ ሌላውን ለመስማት ጆሮ ዳባ ልበስ ያለ ይመስላል፡፡ ጥቂቶች ደግሞ ከታሪክ ተምረን አካሄዳችንን እንድናስተካክል፤ ከስሜት ወጥተን በምክንያታዊነት እንድንነጋገር ዛሬም በብዙ ፍረጃ እና ማሸማቀቅ መሃል ይመክራሉ – አድርባይ፣ አሽቃባጭ፣ ዘረኛ፣ መሃል ሰፋሪ… መባል ሳይገታቸው/ፋቸው አቅጣጫ ይጠቁማሉ፣ መላ ይላሉ፡፡ ሰሚ ግን የለም! ጉልበተኛውም ተመችቶታል፤ የለውጥ ሀይሎችም እነሱ ከያዙት ውጪ ሌላ መንገድ አይታያቸውም ወይም ሌላኛውን መንገድ በመፈረጅ ያርቁታል – ሁሉም ለየራሱ ልክ መሆንን መርጧል፡፡ እውን ይሄ አካሄድ የት ድረስ ይወስደናል??? ነፃነት፣ እኩልነት እና ፍትህ የተነፈገው ህዝባችን የፖለቲካ ድራማችንን ሳይሆን የነፃነት ትግላችን ችግሮቹን ይፈታለት ዘንድ ያስተማራቸው ልሂቃኖቹን ሆደ ሰፊ እና አስተዋይነት የተመላ መሪነት በተስፋ ይጠብቃል፡፡

ከዚህ በኋላም ቢሆን ከፖለቲካ መሪዎች፣ ከአክቲቪስቶችም ሆነ የኔ ብጤ የመብት ታጋዮች የሚጠበቀው ነገር በተመስጦ ማሰላሰል፣ መደማመጥ እና አብሮ ለመስራት እውቅና መሰጣጣት ወሳኝ ነገር ይመስለኛል፡፡ በየትኛውም የፖለቲካ አሰላለፍ ውስጥ እንሁን ከመናናቅ ወጥተን የሁላችን የሆነች ኢትዮጵያን በሁላችን መልካም ፈቃድ እና መተማመን ለመገንባት መከባበር የመጀመሪያው እርምጃችን መሆን አለበት፡፡ የደጋፊ ብዛትና የስሜት መስመር ተከትለን ስም ከመሰጣጣት ተላቀን፤ እኔ ብቻ ልክ ነኝ ከሚል አስተሳሰብ ወጥተን – ሁሉንም ማስተናገድ የሚችል የፖለቲካ ምህዳር የመፍጠር ፍላጎት እና አቅም እንዳለን ከአሁኑ ማሳየት – ለዚህም መነጋገር ይጠበቅብናል፡፡ “የፉክክር ቤት ሳይዘጋ ያድራል” እንደሚባለው ሊያጠፉን የሚሹ ሃይሎች መግቢያ ቀዳዳ እንዳያገኙ ከተራ ብሽሽቅ እና እልኸኝነት ተላቀን፤ ዶግማቲክ የሆነውን ነባር የፖለቲካ ባህል ትተን – እውቅና በመሰጣጣትና በመቀራረብ ቀዳዳዎቹ የሚደፈኑበትን መንገድ መምረጥ ወቅቱ የሚጠይቀን ወሳኝ ጉዳይ ይመስለኛል፡፡

ኢትዮጵያ ለሁሉም፣ ሁሉም ለኢትዮጵያ!
/በአገላለፄ ያስቀየምኩት ሰው ካለ ከልብ ይቅርታ እጠይቃለሁ! ለውይይት፣ ለሙግት እንዲሁም ከተሳሳትኩ ለመታረም ክፍት ነኝ፡፡/
ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ! ዮናታን ረጋሳ

0 comments:

Post a Comment