Sunday 27 September 2015

ነገረ – ኢሕአዴግ- ሥርዓቱ በሁለት ጫፍ የተሳለ አደጋ አፍጦበታል


eprdf two



በብዙ መልኩ ዴሞክራሲያዊ ገፅታን ያልተላበሰው ኢሕአዴግ ራሱን በገዥ መደብነት “አመቻችቶ” አስቀምጧል፡፡ ግንባሩ በቀደመው ዓመት አስረኛ ድርጅታዊ ጉባኤውን በዝግ በማካሄድ እንደተለመደው ባለ ዘጠኝ ነጥብ የአቋም መግለጫ በማውጣት አጠናቋል፡፡ በዚሁ ጉባኤ፣ ከዚህ ቀደም ከተካሄዱ ጉባኤዎች በተለይም በ1994 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ከተካሄደው አራተኛው የድርጅቱ ጉባኤ ጀምሮ ይነሱ የነበሩ አጀንዳዎች ቅርፃቸውን ብቻ በመቀየር ይዘታቸውን እንደጠበቁ እስከ አስረኛው ድርጅታዊ ጉባኤ ድረስ ዘልቀዋል፡፡ በተለይም የመልካም አስተዳደር እጦትና የሙስና ጉዳይ ከድርጅቱ ጋር አብረው የተፈጠሩ እስኪመስሉ ድረስ ችግሮቹ ገንግነዋል፡፡ በ1994ዓ.ም የአዲስ አበባው ጉባኤ አብይ አጀንዳ በመሆን ጉባይተኛው የተወያየበት አጀንዳ “ጥገኛ ዝቅጠት አስተሳሰብ” የስርዓቱ አደጋ መሆኑን ነበር፡፡ የቃላት ሃብታሙ ኢሕአዴግ፣ “ጥገኛ ዝግጠት አስተሳሰብ” የሚለውን ሃረግ “ኪራይ ሰብሳቢ” በሚል አገላለጽ በመተካት በቅርቡ እስከተካሄደው አስረኛ ድርጅታዊ ጉባኤ ድረስ ይህንኑ አጀንዳ ሲመክርበት ኑሯል፡፡ ከግንባሩ ነገረ ታሪክ መረዳት እንደሚቻለውም ድርጅቱ በስልጣን ላይ እስካለ ድረስ ይሄው አጀንዳ (ኪራይ ሰብሳቢነት) ሲነሳና ሲወድቅ እንደሚኖር እሙን ነው፡፡ ርግጥ ይህ ጉዳይ በመንግስት መስሪያ ቤቶች እየታየ ካለው የመልካም አስተዳደር እጦት ጋር በተያያዘ የማታ ማታ የግንባሩን ፍጻሜ የሚያቀርበው ይሆናል፡፡ በርግጥም ግንባሩ እንደሚለው “ኪራይ ሰብሳቢነት የሥርዓቱ አደጋ ነው”፡፡ ከዚህ አኳያ ሥርዓቱ በሁለት ጫፍ የተሳለ አደጋ አፍጦበታል፡፡


“ኪራይ ሰብሳቢነት” ሲባል
ኪራይ ሰብሳቢነት ሲባል ያልተገባ የኢኮኖሚ ጥቅም በማጋበዝ ብቻ የሚተረጎም ሳይሆን ከዚህ ባለፈ የፖለቲካ ጥቅም ትስስር (ኔት ወርክ) እና ቡድንተኝነትን መሰረት ያደረገ የስልጣን መደጋገፍንም የሚጨምር የትርጉም ይዘት አለው፡፡ የአደጋው መንታ መልክም ይሄው ነው፡፡ የስርዓቱ መሪዎች ለማመን በሚከብዱ የሙስና መረቦች በመተብተባቸው በህዝቡ ላይ እየተፈጠሩ ያሉ ቅሬታዎችን መሰረት አድርጎ ሊፈጠር የሚችለው ህዝባዊ አመፅ የአደጋው አንዱ ገጽታ ሲሆን፤ ሁለተኛው የአደጋው መልክ ደግሞ ባለስልጣናቱ እንደ ቡድን በሚዘረጉት የሙስና መረብ ከጥቅም ትስስራቸው ጋር በተያያዘ እንደ መንግስታዊ መዋቅርም ሆነ እንደ ድርጅት የሚመጡ ግምገማዎችን በጋራ የሚመክቱበት እንዲሁም ባለስልጣናቱ የራሳቸውን የቡድን አባል ወደ ተሻለ የስልጣን ከፍታ ለማውጣት የሚያደርጉት ርብርብ የቡድን ፍላጎት የሚታይበት በመሆኑ፣ ፍላጎቱ ከሌላው ቡድን ጋር የሚጋጭ ከሆነ በዚህ መሀል የሚፈጠረው ልዩነት ከስርዓቱ አልፎ ለአገርም አደጋ የሚሆንበት እድል ይኖራል፡፡ በዚህ አግባብ ኢሕአዴግ በሁለት ጫፍ የተሳለ አደጋ አፍጦበታል፡፡ ‘የግንባሩን ቀጣይ እጣ ፈንታ ከሚወስኑት ጉዳዮች አንዱና ዋነኛው ኪራይ ሰብሳቢነት ነው’ የመባሉ እውነታም ከዚህ የመነጨ ነው፡፡ በተለይም የፖለቲካ ኪራይ ሰብሳቢነት አዝማሚያ ብሄርን መሰረት ያደረገ ቡድንተኝነት የሚንፀባረቅበት በመሆኑ አደጋው ጠባብነትን መታያው አድርጎ የሚከሰት ሲሆን ፤ ይህን ተከትሎ የሚፈጠረው ችግር ከሥርዓቱ አልፎ ለአገርም የከፋ መሆኑ የሚያከራክረን ጉዳይ አይደለም፡፡

ስርዓቱ “ኪራይ ሰብሳቢነት ለመታገል ጥረት እያደረኩ ነው” እያለ ዲስኩሩን ቢያሰማም፣ ችግሩ ከመባባሱ ውጭ ጠብ ያለ ለውጥ በአደባባይ ሊታይ አልቻለም፡፡ እጅግ አስደንጋጭ የሙስና ሪከርዶች በተወካዮች ምክር ቤት በኩል በሪፖርት መልኩ ሲታለፍ ማየት የሚደንቅ አይደለም፡፡ በመሬትና በፍትህ አስተዳደር እንዲሁም በመንግስት ንብረት ግዢና ሽያጭ ላይ እየታዩ ያሉ ግልጽ የስልጣን መባለጎችን ስናስተውል አገሪቷን እንደ “መንግስት” እያስተዳደራት ባለው ገዢው ግንባር ላይ እምነት እንድናጣ ያደርገናል፡፡
ባገባደድነው አመት የፌዴራል ዋና ኦዲት መስሪያ ቤት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበው ሪፖርት ሃያ አምስት የሚሆኑ የፌዴራል መስሪያ ቤቶችና ዩኒቨርስቲዎች ህጋዊነት የሌለው የንብረት ግዢና ሽያጭ መካሄዳቸውን፣ ሥራቸውን የለቀቁ ሰራተኞች በሌሉበት እስከ ስድስት ወር የሚደርስ ደመወዝ እንደተከፈላቸው፣ ያለ ጨረታ የኮንስትራክሽን ግንባታ ስራዎች ለተለያዩ ተቋራጮች እንደተሰጠ፣ ህጋዊ የደመወዝ ጭማሪ ላልተደረገላቸው ሰራተኞች በህገ-ወጥ መንገድ ተጨማሪ ክፍያ የከፈሉ መስሪያ ቤቶች መኖራቸውን ያመለከተው ይሄው ሪፖርት፣ በዚህም እንደ አገር ከሶስት ቢሊዮን ብር በላይ ያልተመሳከረ ሒሳብ መኖሩን ይጠቁማል፡፡ ሪፖርቱ የፌዴራል መስሪያ ቤቶችንና የተወሰነ የኒቨርስቲዎችን ብቻ የሚመለከት ሲሆን፤ በየክልሉ ያለውን ምዝበራ ከዚህ ሪፖርት አኳያ ምን ያህል የከፋ ሊሆን እንደሚችል መገመት ይቻላል፡፡ የፌዴራል ዋና ኦዲት መስሪያ ቤት የንብረት ግዢና ሽያጭ ችግር አለባቸው፣ ህጋዊ የፋይናንስ አሰራር አልተከተሉም በሚል በሪፖርቱ የጠቆማቸው የፌደራል መስሪያ ቤቶችም ሆኑ ችግሩ የታየባቸው የዩኒቨርስቲ አመራሮች በህግ ሲጠየቁ ለማየት አልታደልንም፡፡ በርግጥ በኢህአዴግ ቤት ፖለቲካን እንጂ ገንዘብን መሰረቅ የስርዓቱ አንዱ ገጽታ ነውና የተለየ እርምጃ አይጠበቅም፡፡ ይሁንና እነዚህ ከፍተኛ አመራሮች ከገንዘብ ባለፈ የፖለቲካ ፍንገጣ ያሳዩ ቀን ‘ፋይላቸው’ ከመሳቢያ መውጣቱ አይቀሬ ነው፡፡

በኢህአዴግ ቤት፣ ከሁሉም የሙስና አይነቶች ከባዱ ሙስና የመሬት ወረራን ተከትሎ እየተፈጠረ ያለው ምዝበራ ዋናው ተጠቃሽ ነው፡፡ በዚህ ዘርፍ እየታ ያለው ሙስና “ውሻ በቀደደው ጅብ ይገባል” እንዲሉ የከፍተኛ አመራሮችን ፈለግ በመከተል ቀበሌ ድረስ ያሉ አመራሮች “ከድርሻቸው” በላይ በወዳጅ ቤተ ዘመድና በሙታን ስም ሳይቀር የመሬት ወረራዉን ተያይዘውታል፡፡ የታችኛው አመራር ምዝበራ አይን እያወጣ በመምጣቱ “ኪራይ ሰብሳቢነትን አየተዋጋሁ ነው” የሚለው ኢሕአዴግ፣ ለአስመሳይ ፖለቲካው ማሳያ ይሆን ዘንድ አልፎ አልፎ የታችኛውን አመራር ጭዳ ሲያደርገው ይታያል፡፡ ነገሩ ‘የኪራይ ሰብሳቢዎች መተካካት’ አይነት ነገር ነው፡፡ የበላ ይሻራል፡፡ ያልበላ ይሾማል፡፡ ኡደቱም በዚህ መልኩ እየቀጠለ ያለ ይመስላል፡፡ ለዚህ ማሳያ ሆኖ የሚቅበው ጉዳይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተሞክሮ ነው፡፡ የከተማ አስተዳደሩ የከተማ ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ምክትል ኃላፊ የሆነው አቶ ኃየሎም ጣውዩ በነሐሴ ወር ሦስተኛ ሳምንት ለንባብ ከወጣው ከሪፖርተር ጋዜጣ ጋር ባደረገው ቃለ መጠየቅ በ2007 የሥራ ዘመን ከመሬት ጋር በተያያዘ ብቻ በየደረጃው ያሉ 315 (ሦስት መቶ አስራ አምስት) አመራሮችና ፈፃሚዎች ከኃላፊነታቸው እንደተነሱ፣ ከእነዚህ ውስጥ በህግ የሚጠየቁ ኃላፊዎች እንዳሉ ተናግሯል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ከተማ አስተዳደሩ 221 (ሁለት መቶ ሃያ አንድ) አመራሮችንና 4100 (አራት ሺህ አንድ መቶ) የሚሆኑ የመንግስት ሰራተኞችን ከሥራ ሊያሰናብት እንደሆነ፣ በህግ የሚጠየቁ መኖራቸውንም ለፋና ብሮድ ካስት አስታውቋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ የካቢኔ ሹም ሽር እስከማድረግ የሚደርስ እርምጃ ሊወስድ እንደሆነም መረጃዎች በመውጣት ላይ ይገኛሉ፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ መካከለኛ አመራሮች ከሙስና ጋር በተያያዘ ከሥራ የሚሰናበቱበት አዲስ አበባ እንደ ትናንቱ ሁሉ ዛሬም ‘አንገት አልባ’ አመራሮችን ተሸክማ በማዝገም ላይ ትገኛለች፡፡ ነገሩ “ጉልቻ ቢቀየር …..” አይነት ነገር ነው፡፡ የበላ ይሻራል፡፡ ያልበላ ይሾማል፡፡ ዑደቱም ይቀጥላል….

ከመሬት ወረራ ጋር በተያያዘ በተለይም ሀሰተኛ የመሬት ባለይዞታነት መረጃ በማዘጋጀትና ህጋዊ ቅድመ ሁኔታ ላላሟሉ ሰዎች በጥቅም ትስስር መሬት የመስጠቱ ሁኔታና የአመራሩ የመሬት ቅርምት ከአዲስ አበባ ከተማ በከፋ መልኩ በሌሎች የክልል ከተሞች እንዳለ ከአንባቢ የተሰወረ አይደለም፡፡ በፍትህ አስተዳደር በኩልም አስደንጋጭ የሙስና ተግባር እየተከሰተ እንዳለ የአደባባይ ምስጢር ነው፡፡ ከ30 ሺህ እስከ 350 ሺህ ብር የሚደርስ ገንዘብ በመቀበል በሀሰተኛ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ፍርደኞችን የለቀቁ የፌደራልና የክልል ማረሚያ ቤቶች መካከለኛ አመራሮችን እንዲሁም ከሙስና ጋር በተያያዘ የዳኞችን ክስ/ስንብት መስማት ከአመት አመት እየተለመደ መጥቷል፡፡ እንግዲህ በ”ሕግ በምትመራ” አገር ላይ ከአመት አመት አስደንጋጭ የሙስና ዜናዎችን በሪፖርትም፣ በክስም መልክ እየታየ በመሆኑ “መንግስት” የሚባለው አካል ምን እየሰራ እንዳለ መጠየቅ ግድ ይለናል፡፡ የመሬትና የፍትህ አስተዳደርን እንደ ማሳያ አንስተን ተመለከትን እንጂ በሌሎች መንግስታዊ ተቋማቶች ዘንድ ምን አይነት ጉድ ሊፈጸም እንደሚችል መገመት የሚከብድ አይደለም፡፡ በቅርቡ እንኳ የኦሮሚያ ክልል ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ የነበረው አቶ ወንድሙ ቢራቱ በሙስና ወንጀል ተጠርጥሮ የ500 (አምስት መቶ) ሚሊዮን ብር ኦዲት እየተጣራበት ይገኛል፡፡ የምርመራው ውጤት ምን ይሁን ምንም አንድ የክልል ከፍተኛ ባለስልጣን በዚህን ያህል የብር መጠን በሙስና ወንጀል መጠርጠሩ (ኦዲት መደረጉ) ሥርዓቱ በምን ያህል መጠን እንደ ነቀዘ ጥሩ ማሳያ ይሆነናል፡፡

በየአመቱ ተዝቆ ከማያልቁ መንግስታዊ ጉዶች መካከል ጥቂቱን ቆንጥሮ የሚያሳየን የፌደራል የስነ-ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እንቅስቃሴ ከአሳ ነባሪዎች ይልቅ ትንንሽ አሳዎች ላይ ትኩረት አድርጎ “መረቡ”ን የጣለ በመሆኑ፣ አህአዴግ ስልጣን ላይ እስካለ ድረስ ሙስና የምንግዜም ቀዳሚ አጀንዳ ሆኖ ይኖራል፡፡ ገዢዉ መደብ ኢህአዴግ፣ በጉምቱ ባለሥልጣናቱ ላይ የሚታየውን ሙስና ከመቅረፍ ይልቅ “ሂስና ግለ ሂስ” በሚል ድርጅታዊ ቀኖናዉ ለጉዳዩ ከሚያሳየው መለሳለስ የተነሳ የሙስና ጉዳይ ለፖለቲካዊ አለመግባባቶች የመፍትሄ ማፈላለጊያ እየሆነ መጥቷል፡፡ ግንባሩ እንደሁልጊዜው ሁሉ በአስረኛ ድርጅታዊ ጉባኤው “የፖለቲካዊ ኢኮኖሚ ኪራይ ሰብሳቢነት ሚናን በልማታዊ አስተሳሰብ በመተካት የኢትዮጵያን ሕዳሴ እናረጋግጣለን” ቢልም፣ ጉዳዩ ከተለመደው የአቋም መግለጫነት የዘለለ ጠብ የሚል ነገር እንደማይኖረው የድርጅቱ የቀደመ ተሞክሮ ይነግረናል፡፡

እንደ-መዉጫ
በመቶ ብሮች የሚቆጠር የወር ደመወዝተኛ በበዛባት አትዮጵያ፣ በየመስሪያ ቤቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ብር ምዝበራ መካሄዱን፣ ይህን ተከትሎ እንደ አገር ቢሊዮን ብሮች በየዓመቱ በመንግስት ሌቦች መመዝበሩን የሚያመለክቱ ሪፖርቶች ከመንግስታዊ ተቋማት ጭምር መስማት መደበኛዉን የትራፊክ አደጋ ሪፖርት የመስማት ያህል እንኳን አላስደነግጠን ብሏል፡፡ በፖለቲካና በነጻ ተቋምነት መሃከል የዋልሉ ተቋማት አሁን አሁን የጠቅላዩ ኢህአዴግ ክንፍ መሆናቸዉን በተግባር እያሳዩን ነዉ፡፡ መንግስት በከሳሽነት በሚቀርብባቸዉ ፖለቲካ-ቅብ የክስ ጉዳዮች ተሸናፊ ሆኖ የታየበት አጋጣሚ የለም፡፡ የፍርድ ቤት ዉሳኔ በማረሚያቤት አመራሮች ሳይፈጸም ሲቀር የታዘብንባቸዉ አጋጣሚዎች ከጣቂት በላይ ናቸዉ፡፡ “ፍትህ”ን በብረትና በገንዘብ የገዙ አካላት አንገታቸዉን ቀና አድርገዉ በሚሄዱባት ኢትዮጵያ፣ የግፉአን ድምጽ በርክቶባታል፡፡ ጎን ማሳረፊያ ያጡ ዜጎች በበረከቱባት ሃገር፣ ከግማሽ ደርዘን በላይ ቪላ ቤቶች በተለያዩ ግለሰቦች ስም ያለዉ የኢህአዴግ መካከለኛ አመራር ፈልጎ ማግኘት ያን ያህል የሚከብድ አይደለም፡፡ በቦታ ርቀት፣ በግንዛቤ ማነስ፣ ከበቂ የምግብ አቅርቦት እጦት ጋር በተያያዘና መሰል ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ችግሮች የተነሳ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ህጻናትና ወጣቶች በየአመቱ ትምህረታቸዉን ለማቋረጥ በሚገደዱባት አትዮጵያ፣ ልጆቻቸዉን ከአንድ ቀበሌ የግማሽ አመት በጀት ጋር የሚስተካከል የዉጭ አገር ትምህርት ቤት የሚያስተምሩ የአህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣናት ቁጥር እንደ ኢኮኖሚ “እድገቱ” ሁሉ በሁለት አሃዝ የሚገለጹ ናቸዉ፡፡ ንጹህ የመጠጥ ዉሃ ያጣ ህዝብ በበረከተባት አገር፣ የአልኮል መጠጥ ፋብሪካ በአክሲዮን ስም የገነቡ፤ ሚለዮኖች የዕለት ጉርሳቸዉን በጡበት ሁኔታ የግል ባንክ ባለቤት የሁኑት ባለስልጣናት የደም እንጀራ እየጎረሱ እንደሆነ ሊረዱት አልቻሉም፡፡

የኢህአዴግ ባለስልጣናትን ነገረ-ስራ በቅጡ ያስተዋለ ሰዉ የሚከተለዉ ድምዳሜ ላይ መድረስ ይቻለዋል፡፡ እርሱም፡- ‘ማንኛዉም የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣናት ከህግ በላይ ናቸዉ፡፡ የትኛዉም የህዝብም ሆነ የአገር ሃብት የባለስልጣናቱ እንጂ የህዝብ አይደለም’ ባልተጻፈ ህግ እየተተገበረ ያለዉ እዉነታ ይህ ነዉ፡፡ ኢህአዴግ “የ አስራ ሦስት ወር ጸጋ” የተባለላትን አገር ወደ አስራ ሦስት ወር የፖለቲካ ጭቆናና የኢኮኖሚ ብዝበዛ አሻግሯታል፡፡ የአገሪቱ ማህበራዊ ቀዉስ ሲጨምር እንጂ ሲቀንስ አላየንም፡፡ አይነ ስዉሩን ደርግ ሸኝተን ደንቆሮዉን አህአዴግ ተክተናልና ዛሬም እንደ ትላንቱ በደል የማንነት አካል ሆኗል፡፡ አስር፣ እንግልት፣ ስቅየት፣ ስደት፣ ሞት … ከገዥዉ መደብ በተቃራኒ የተሰለፉ ኢትዮጲያዉያን እጣ ፋንታ መሆኑን ሩብ ክፍለ-ዘመን ያካለለዉ የአገዛዙ ተሞክሮ ጮሆ ይመሰክራል፡፡ ገዥዉ መደብ በብዙ መልኩ ኮረብታዉ እርቆት ቁልቁለቱን በሚገርም ፍጥነት ተያይዞታል፤ የአይቀሬዉን አብዮት ማፍጠኛ የተጫነዉ ኢህአዴግ የህልዉናዉ ማክተሚያ ጊዜ ሩቅ አይደለም፡፡ በየአመቱ እንደ “መንግስት” አዋጂ አዲስ ዓመት መግባቱን በሚዲያ ስንሰማ ኑረናል፡፡ አዲስ ነገር በማናይበት ሁኔታ “አዲስ ዓመት” ብሎ ነገር ምናችን ነዉ?! እኛ ኢትዮጵያዊያን አዲስ አመት ሳይሆን አዲስ ስርዓት እንሻለን!!

(የዚህ ጦማር አቅራቢ ጋዜጠኛ ሙሉዓለም ገ/መድህን ሲሆን በቅርቡ “የኢሕአዴግ ቁልቁለት” በሚል ርዕስ የጻፈው መጽሀፍ ለንባብ በቅቷል፡፡ ይህ ጽሁፍ በተለይ ለጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ የተላከ ነው፡፡)

 Source:: Goolgule
ሦስቱ ከፍተኛ አመራሮች ከአገር ውጭ ናቸው
የኦሮሚያ የኅብረት ሥራ ባንክ ፕሬዚዳንት፣ ሁለት ምክትል ፕሬዚዳንቶችና የባንኩ ዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር፣ ምክትል የቦርድ ሊቀመንበርና የዓለም አቀፍ የባንክ አገልግሎት ኃላፊ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ሰሞኑን ከኃላፊነታቸው ከታገዱ በኋላ፣ ያልታገደው ቀሪው ቦርድ ባንኩን የሚመሩ አዳዲስ አመራሮችን ሰየመ፡፡
በብሔራዊ ባንክ ትዕዛዝ ከኃላፊነታቸው የታገዱት የቦርድ ሊቀመንበሩ የቀድሞው የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር አበራ ደሬሳ፣ ምክትል ቦርድ ሰብሳቢው አቶ ታደሰ መስቀላ፣ ፕሬዚዳንቱ አቶ ወንድማገኘሁ ነገራ፣ ምክትል ፕሬዚዳንቶች አቶ ቶሎሳ በየነና አቶ አበበ ጥላሁን፣ እንዲሁም የዓለም አቀፍ ባንክ አገልግሎት ዳይሬክተሩ አቶ ባንታየሁ ከበደ ናቸው፡፡
ከባንኩ የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው፣ ከብሔራዊ ባንክ የወጣው የዕገዳ ደብዳቤ በኋላ ዕገዳው ያልተመለከታቸው ቀሪዎቹ የቦርድ አባላት በመሰብሰብ አቶ በላቸው ሁሪሳን የቦርድ ሊቀመንበር፣ አቶ ዳኛቸው ሽፈራውን ምክትል ሊቀመንበር አድርጎ ሰይሟል፡፡ በአቶ ወንድማገኘሁ ምትክ አቶ ሙሉነህ ዲሳሳን ጊዜያዊ ፕሬዚዳንት አድርጓል፡፡ አቶ ሙሉነህ የባንኩ የፊንፊኔ ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ በመሆን ሲያገለግሉ የነበሩ ናቸው፡፡ የባንኩ የዓለም አቀፍ ባንክ አገልግሎት ዳይሬክተር ሆነው ሲያገለግሉ በነበሩት በአቶ ባንታየሁ ምትክ ደግሞ የባንኩ የገቢና ወጪ ንግድ ዳይሬክተር በመሆን በማገልገል ላይ የነበሩት አቶ ፍፁም ሐዋስ ተመድበዋል ተብሏል፡፡ አቶ ፍፁም ግን ይህ ሪፖርት እስከተጠናከረበት ጊዜ ድረስ ደብዳቤ እንዳልደረሳቸው ቢገልጹም፣ ለቦታው መታጨታቸውና ሥራውን እየሠሩ መሆኑ ታውቋል፡፡
በታገዱት ምክትል ፕሬዚዳንቶች ምትክ ደግሞ አቶ ፈየራ አጀታና አቶ ግዛው ኃይሉ ተመድበዋል፡፡ አቶ ፈየራ ቀደም ብሎ የሀብትና አገልግሎቶች ስትራቴጂና ለውጥ ኃላፊ ነበሩ፡፡ አቶ ግዛው ደግሞ የደንበኞች ሒሳብና የቅርንጫፎች ማስተባበሪያ የሥራ ሒደት መሪ ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩ ናቸው፡፡
በባንኩ ውስጥ ተፈጽሟል በተባለ በውጭ ምንዛሪ ላይ በተፈጸመ የአሠራር ግድፈት በብሔራዊ ባንክ ከታገዱት አመራሮች ውስጥ ዶ/ር አበራ ዴሬሳ፣ አቶ ወንድምአገኘሁ ነገራና አቶ ታደሰ መስቀላ አገር ውስጥ እንደሌሉ፣ የዕገዳው ደብዳቤ የወጣባቸውም በሌሉበት እንደሆነ የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡ እንደ ምንጮች ገለጻ ከሆነ የኦሮሚያ ቡና አምራቾች አርሶ አደሮች የኅብረት ሥራ ማኅበር ሊቀመንበር የሆኑት አቶ ታደሰ ከቦርዱ ኃላፊነታቸው ቀደም ብለው ወጥተው ነበር፡፡ አወጣጣቸው ከቀሪዎቹ ቦርድ አባላት ጋር ባለመስማማት ነው ተብሏል፡፡
ከኦሮሚያ የኅብረት ሥራ ባንክ አካባቢ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ ሦስቱ ከፍተኛ ኃላፊዎች የብሔራዊ ባንክ ዕገዳ ደብዳቤ ከመውጣቱ በፊት ለሥራ ወደ ውጭ ሄደዋል፡፡
እንደ ምንጮች ገለጻ የባንኩ ከፍተኛ አመራሮች ሊታገዱ የቻሉት ከብሔራዊ ባንክ መመርያ ውጪ ከውጭ ምንዛሪ ግብይት ጋር በተያያዘ ነው፡፡ የባንኩ የውጭ ምንዛሪ ግብይት ከሌሎች ባንኮች በተለየ ከፍተኛ እንደነበር የሚያስታውሱት ምንጮች፣ ከመመርያ ውጪ የሚደረግ ግብይት ተፈጽሟል ተብሎ በባንኩ ላይ ምርመራ ሲደረግ ቆይቷል፡፡
ብሔራዊ ባንክ ከመመርያና ከደንብ ውጪ የተካሄደ ግብይት ነበር የሚለውን ፍንጭ በመያዝ በባንኩ ላይ ጥልቅ ምርመራ ሲያካሂድ መቆየቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡ አመራሮቹን ካገደ በኋላም ምርመራውን የቀጠለ ሲሆን፣ በቀጣይ ወደ ሕጋዊ ዕርምጃዎች ሊገባ እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡ የኦሮሚያ የኅብረት ሥራ ባንክ በአሁኑ ወቅት ካሉት 16 የግል ባንኮች መካከል፣ በጥቂት ዓመታት ልዩነት በዓመታዊ የትርፍ መጠኑና ከፍተኛ የትርፍ ክፍፍል በማስገኘት በሦስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ የቻለ ነው፡፡
ከሦስት ዓመታት በፊት በባንኮች የትርፍ መጠን የደረጃ ሠንጠረዥ ስምንተኛ ደረጃ ላይ የነበረው ባንክ፣ በተለይ ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ ደረጃውን ከዳሸንና ከአዋሽ ባንኮች ቀጥሎ በሦስተኛ ደረጃ ላይ ሊቀመጥ ችሏል፡፡
ባንኩ በ2006 በጀት ዓመት ከታክስ በፊት 475 ሚሊዮን ብር ያተረፈ ሲሆን፣ የ2007 በጀት ዓመት ግርድፍ የፋይናንስ ሪፖርቱ የሚያመለክተው ደግሞ ከታክስ በፊት 602 ሚሊዮን ብር ማትረፍ መቻሉን ነው፡፡
በ2006 በጀት ዓመት ግን ባንኩ ትርፍ ካስመዘገበባቸው የሥራ ዘርፎች ሁሉ ብልጫ የነበረው የዓለም አቀፍ የባንክ አገልግሎት ነበር፡፡ ከግል ባንኮች ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ከያዙ ጥቂት ባንኮች መካከል አንዱ ሆኖ ቆይቷል፡፡ አሁንም ለባንኩ የሥራ ኃላፊዎች መታገድ ምክንያት ከዚህ የውጭ ምንዛሪ ክምችት አመጣጥ ጋር የተያያዘ ነው ተብሏል፡፡ አዲስ የተሰየመው የዳይሬክተሮች ቦርድም በምክትል ፕሬዚዳንቱ ላይ የጻፈው አዲስ ደብዳቤ ይህንኑ የሚያመለክት ነው፡፡
ብሔራዊ ባንክ በአቶ ጥላሁን ላይ ዕገዳ ከጣለ በኋላ በአዲሱ በቦርድ ሰብሳቢ አቶ በላቸው ሁሪሳ ተፈርሞ የወጣው ደብዳቤ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በኦሮሚያ ኅብረት ሥራ ባንክ ላይ ባደረገው ልዩ ምርመራ ውጤት ላይ በመንተራስ፣ የባንኩ ዳይሬክተሮች ቦርድ ልዩ ግብረ ኃይል አቋቁሞ ጥልቅ ምርመራ ማድረጉን ይገልጻል፡፡ በዚህ ባደረገው ጥልቅ ምርመራ ውጤት ላይ በመመርኮዝ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የወሰነው ውሳኔ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ የባንኩ ዳይሬክተሮች ቦርድ መስከረም 5 ቀን 2008 ዓ.ም. እንዳሰናበታቸው፣ ከመስከረም 12 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ደግሞ ከባንኩ እንደተሰናበቱ የሚያስታውቅ ደብዳቤ ነው፡፡
ይህ ደብዳቤ የባንኩ ቦርድ ቀደም ብሎ የወሰነው መሆኑን ቢያመለክትም፣ የብሔራዊ ባንክ ዕገዳ ተፈጻሚ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ሪፖርተር ማብራሪያ ለማግኘት ቢሞክርም አልተሳካም፡፡
በታገዱት የቦርድ ሰብሳቢ ምትክ የተተኩት አቶ በላቸው ሁሪሳ ቦርዱን በአባልነት ሲያገለግሉ የቆዩ ሲሆን፣ ኢሌምቱ ኢንተግሬትድ የተባለውን አክሲዮን ማኅበር (ኢሌምቱ ወተት) ቦርድ ሊቀመንበር ናቸው፡፡ የኦሮሚያ የኅብረት ሥራ ባንክ በአብዛኛው የኅብረት ሥራ ማኅበራትንና ዩኒየኖችን በአክሲዮን አባልነት ያቀፈ ሲሆን፣ አገልግሎቱም ከእነዚሁ ማኅበራት ጋር የተያያዘ እንዲሆን ታስቦ የተቋቋመ ነው፡፡
ባንኩን በቦርድ ዳይሬክተርነት ሲመሩ የቆዩትና በብሔራዊ ባንክ የታገዱት ዶ/ር አበራ ደሬሳ በግብርና ሙያ የሚታወቁና የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ በመሆን ማገልገላቸው ይታወሳል፡፡
- See more at: http://www.satenaw.com/amharic/archives/10510#sthash.VHvkfaw7.dpuf

0 comments:

Post a Comment