Wednesday 19 March 2014

የአዳማ ከተማ የአንድነት ፓርቲ ሰብሳቢ ወጣት ምርቱ ጉታ ታሰረ

በጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ ስም ለተሰየመውና “ግጥም ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል በዚህ ወር መጨረሻ በአዳማ ለሚደረገው የኪነጥበብ ምሽት የተዘጋጀውን የርዕዮት ምስል ያለበት የፖስተር ንድፍ በእጁ ይዞ በመገኘቱ ተጨማሪ ምርመራ እየተደረገበት ነው፡፡
——————————-
በአዳማ ከተማ የአንድነት ፓርቲ ሰብሳቢ የሆነው ወጣት ምርቱ ጉታ ዛሬ መጋቢት 10 ቀን 2006 ዓ.ም ከጠዋቱ 3፡30 ገደማ በተለምዶ ዠቅአለ ተብሎ በሚጠራው ገበያ አካባቢ መታሰሩን የከተማዋ የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወጣት ተስፋዬ ዋቅቶላ ለፍኖተ ነፃነት ገለፀ፡፡
Mertu Guta
Mertu Guta
የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው እንደገለፀው ዠቅአለ ተብሎ በሚጠራው ገበያ አካባቢ የሚገኙ አነስተኛ ነጋዴዎች የገበያ ስፍራው እንዲለቁ መጠየቃቸውን ተከትሎ ሲያሰሙ የነበረውን ብሶት እንደዜጋ ለማዳመጥ ከሞከሩ የአንድነት አባላት መካከል ወጣት ምርቱ ጉታን አስረውታል፡፡
ወጣት ምርቱ ጉታ በአሁኑ ሰዓት በአዳማከተማ ፖሊስ መንሪያ የወረዳ4 ፖሊስ ጽ/ቤት ውስጥ እንደሚገኝ የታወቀ ሲሆን በአዳማ ከተማ የአንድነት ጽ/ቤት ለማሰራጨት የተዘጋጀውን በራሪ ወረቀትና “ግጥም ለነፃነት” በሚል መሪቃል በአዳማ የአንድነት ጽ/ቤት በወሩ መጨረሻ ለሚዘጋጀው የኪነጥበብ ምሽት የተዘጋጀውን የፖስተር ንድፍ በእጁ ይዞ በመገኘቱ ተጨማሪ ምርመራ እየተደረገበት መሆኑ ታውቋል፡፡
የአዳማ ከተማ የአንድነት ፓርቲ “ግጥም ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል በጽ/ቤቱ በወሩ መጨረሻ የሚያደርገውን የኪነጥበብ ምሽት የከተማው ተወላጅ ለሆነችውና በህገወጥ እስር ለምትገኘው ለርዕዮት አለሙ መታሰቢያ እንደተሰየመ የከተማዋ የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወጣት ተስፋዬ ዋቅቶላ ለፍኖተ ነፃነት ጨምሮ ገልጧል፡፡

Source:-  Fenote Netsanet

0 comments:

Post a Comment