Wednesday 8 January 2014

ከኦነግ ጋር በተያያዘ ክስ ከተመሰረተባቸው መካከል 45ቱ በእስራት ተቀጡ


በትምህርት ተቋማት ላይ ቦምብ በማፈንዳት፤ በፊንጫ ስኳር ፋብሪካ ላይ በደረሰው የ2 ሚሊዮን ብር ዝርፊያ በመሳተፍ፣ አብያተ-ክርስቲያናትን በማቃጠል፣ አባላትን በመመልመልና አመፅ በማነሳሳት የኦሮሚያ ፌዴሬሽንን ከህገ-መንግስቱ ተቃራኒ በሆነ መንገድ ከኢትዮጵያ ግዛት ለመገንጠል ሲንቀሳቀሱ ይዣቸዋለሁ ሲል የፌዴራሉ ዐቃቤ ሕግ ክስ ከመሰረተባቸው 69 ተከሳሾች
መካከል 45ቱ ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው ከ3 እስከ 12 ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራት ሲቀጡ 18 በነፃ ተሰናበቱ።

የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት ከትናንት በስቲያ (ሰኞ) ባስቻለው ችሎት፤ የፈፀሙት ድርጊት በንባብ ሲቀርብ እንደተሰማ ነው ተከሳሾቹ በኬኒያ፣ በሶማሊያና በኤርትራ በመዘዋወር የጦር ስልጠናን በመውሰድና የአባላትን ቁጥር ለመጨመር ከመስራት በተጨማሪ በሀገር ውስጥና በውጪ ከሚገኙ ሰዎች የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ወይም ኦነግ ለተሰኘውና መንግስት አሸባሪ
ብሎ በሰየመው ቡድን ስም የገንዘብ ዝውውር ሲያደርጉ እንደነበር ተዘርዝሯል።

በተለይም 1ኛ ተከሳሽ ተሻለ በከሺ፤ በ1998 ዓ.ም በፊንጫ ስኳር ፋብሪካ ላይ በተካሄደው ዝርፊያ ከግብረአበሮቹ ጋረ በመሳተፍ መንግስት 2 ሚሊዮን ብር እንዲያጣ ከማድረጉም በተጨማሪ በአንድ ትምህርት ቤት ላይ ቦምብ በመወርወር ወንጀል ጥፋተኛ ተብሏል። ሌላኛው ተከሳሽም በኦሮሚያ ቆሬ መንደራደዩ በሚባል አካባቢ ከኦነግ አባል በተሰጠ ትዕዛዝ በ1996 ዓ.ም
አብያተ ክርስትያናትን አቃጥለው ሰው ገድለዋል ሲል ዐቃቤ ሕግ የክስ ዝርዝሩን ያስረዳል። ተከሳሾቹ መንግስትን በኃይል ለመገልበጥ በማሴር፤ ገንዘብ በማሰባሰብና መሳሪያ በመግዛት፤ አባላትን በመመልመልና በራሪ ወረቀቶችን
በማዘጋጀት የሽብር ቡድኑን አላማ በመደገፍ ሲንቀሳቀሱ ነበር ሲል ዐቃቤ ሕግ ያስረዱልኛል ያላቸውን ከሃምሳ በላይ የሰውና የሰንድ ማስረጃዎችን ለፍርድ ቤት አቅርቧል።

የግራ ቀኙን ሀሳብ ሲመረምር የቆየው ፍርድ ቤቱ፤ ተከሳሾቹ የፈፀሙትን ወንጀል ያብራራው የዐቃቤ ሕግ የክስ መዝገብ የደረሰውን ውድመት በዝርዝር የሚያሳይ ካለመሆኑ መነሻነት የወንጀሉን ደረጃ መካከለኛ ነው ሲል
ያስቀመጠው ሲሆን፤ ይህም ቢያንስ እስከ 15 ዓመት ፅኑ እስራት ያስቀጣ እንደነበር በማስታወስ ተከሳሾቹ ያቀረባቸውን በርካታ የቅጣት ማቅለያዎች ከግምት ውስጥ በማስገባት የቅጣት ውሳኔው መዘጋጀቱን አትቷል።

ሰኞ ዕለት የቅጣት ውሳኔውን ያስተላለፈው የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎትም ዐቃቤ ሕግ ያቀረባቸውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች በአግባቡ ካየ እና የተከሳሾቹንም የመከላከያ ማስረጃዎችና የቅጣት ማቅለያዎችን
ከመረመረ በኋላ ቀደም ላለው ጊዜ 18 የሚሆኑትን ተጠርጣሪዎች ነፃ ናችሁ ሲል በብይን ያሰናበታቸው ሲሆን፤ የሁለት ተከሳሾች ጉዳይ ደግሞ ለብቻው ተነጥሎ በመታየት ላይ ነው ሲል አስረድቷል። በተቀሩት 45 ተከሳሾች ላይም
የጥፋተኝነት ውሳኔ ካስተላለፈ በኋላ ከ3 እስከ 12 ዓመታት በሚደርስ ፅኑ እስራትና 40 በሚደርሱት ላይም ከ2 እስከ 3ዓመት የሚደርስ የህዝባዊ መብት እገዳ ጥሎባቸዋል።

ሰንደቅ ጋዜጣ

0 comments:

Post a Comment