Friday 15 December 2017

ተከሳሾች በዳኛ ዘርዓይ ወልደሰንበት ላይ ያቀረቡት ተቃውሞ ውድቅ ተደረገ

"ዳኛው አማራ በማንነቱ የማይኮራ፣ በጎጥ የሚጠራ ህዝብ ነው በማለት ሰፊ የዘረኝነት አስተሳሰብ አራምደዋል። እኛ አማራ ስለሆንን ፍትሃዊ ዳኝነት ይሰጡናል ብለን አናምንም" ተከሳሾች

" ዳኛው አማራ በዘሩ የማይኮራ፣ በጎጥ የሚጠራ ህዝብ ነው ማለታቸው ከተከሳሾች ጉዳይ ጋር አይገናኝም" ፍርድ ቤቱ

"ህገ መንግስቱ የሰጠኝ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብቴ ነው" ዳኛ ዘርዓይ ወልደሰንበት

(በጌታቸው ሺፈራው)

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4 ወንጀል ችሎት ዛሬ ታህሳስ 6/2010 በአማራ ህዝብ ላይ የዘረኝነት አስተሳሰብ አራምደዋል በሚል በተከሳሾች አቤቱታ የቀረበባቸው የችሎቱ የግራ ዳኛ ዘርዓይ ወልደሰንበት በችሎት እንዲቆዩ ወስኗል።

በእነ ብርሃኑ ሙሉ ክስ መዝገብ የተከሰሱ አራት የአማራ ተወላጆች ዳኛ ዘርዓይ በወልቃይት ጉዳይ ላይ በፃፉት ሰፊ ፅሁፍ "አማራ በማንነቱ የማይኮራ፣ በጎጥ የሚጠራ ህዝብ ነው። ……" የሚል ከትግራይ ህዝብ ጋር በማነፃፀር ሰፊ የዘረኝነት አስተሳሰብ በማራመዳቸው፣ ተከሳሾችም አማራ በመሆናቸው ዳኛው በዚህ አስተሳሰባቸው ፍትሃዊ ዳኝነት እንደማይሰጧቸው በመግለፅ ከችሎት እንዲነሱ ተቃውሟቸውን አቅርበዋል። ተከሳሾቹ አዋጅ 25/1988 አንቀፅ 27 (1) ከሀ እስከ ያሉትን ድንጋጌዎች በመጥቀስ ተቃውሞ የቀረበባቸው ዳኛ በግድ እዳኛለሁ ስለማይሉ ራሳቸውን ከችሎት እንደሚያነሱ በአቤቱታቸው ላይ ጠቅሰዋል።

ሆኖም ዳኛው በአቤቱታው መሰረት ራሳቸውን ያላነሱ ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱ ዳኛ ዘርዓይ በቀረበባቸው አቤቱታ ላይ መልስ እንዲሰጡ ፈቅዶላቸዋል። በዚህም መሰረት ዳኛ ዘርዓይ በአማራ ህዝብ ላይ አራምደውታል የተባለው አስተሳሰብን ህገ መንግስቱ የሰጠኝ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብቴ ነው የሚል መልስ ሰጥተዋል። ፍርድ ቤቱም( በቀሪ ሁለት ዳኞች) ዳኛ ዘርዓይ ወልደሰንበት ሆርን አፍየርስ ላይ የፃፉትንና በስፋት የዘረኝነት አስተሳሰብ አራምደውበታል የተባለውን ፅሁፍ እና ዳኛው ለአቤቱታው የሰጡትን መልስ በቀሪ ዳኞች መርምሬያለሁ ብሏል።

በዚህም መሰረት ዳኛው ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብታቸውን ተጠቅመው የሰጡት ሀሳብ ነው፣ ከተከሳሾቹ ጉዳይ ጋርም አይገናኝም በሚል የተከሳሾቹን አቤቱታ ውድቅ አድርጎታል። ፍርድ ቤቱ የሚቀርቡት አቤቱታዎች ህጋዊ መሆናቸውን ገልፆ፣ ነገር ግን በዳኛው ላይ የሚቀርቡት አቤቱታዎች የዳኛውን መብት የሚጋፉ እንዳይሆኑ ጥንቃቄ ያስፈልጋል የሚል ማሳሰቢያ ሰጥቷል።


የወልቃይት አማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ አባላትን ጨምሮ "ሽብር" ክስ የቀረበባቸው ሌሎች አማራ ተከሳሾችም በዳኛው ላይ ተመሳሳይ አቤቱታ አቅርበው ዳኛው ይነሳ አይነሳ የሚለውን ለመወሰን ቀጠሮ የተሰጣቸው ሲሆን የእነ የእነ ብርሃኑ ሙሉ በጉዳዩ ላይ ብይን የተሰጠበት የመጀመርያ መዝገብ ሆኗል።

0 comments:

Post a Comment