Monday 10 February 2014

«አሁን ባለንበት ሁኔታ ውህደት የሚባል ነገር ቦታ የለውም» የሰማያዊ አመራር አባል


የሰማያዊ ፓርቲ ከፍተኛ አመራርና የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊዉ ወጣት ብርሃኑ ተክለ ያሬድ ድርጅታቸው «ውህደት ፈጽሞ አያስፈልግም ብሎ የማያምን እንደሆነ የገለሱ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ግን ዉህደት እንደማይታሰብ አሳወቁ። ፓርቲዉ ከሌሎች ድርጅቶ ጋር አብሮ ለመስራት እና ለመዋሃድ ፈጽሞ የተዘጋ በር እንደሌለው የገለጹት አቶ ብርሃኑ ከዉህደት በፊት ግን መቅደም ያላባቸው ጉዳዮች (የቤት ስራዎች) እንዳሉ ይናገራሉ።
መሰራት ያላባቸውን የቤት ሥራዎች ምን እንደሆነ አቶ ብርሃኑ በጽሁፋቸ ያልገለጹ ሲሆን፣ «አሁን ባለንበት ሁኔታ ውህደት የሚባል ነገር ቦታ የለውም» ሲሉ የቤት ሥራቸዉን የሰሩ ደርጅቶች እንደሌሉ በማመላከት የሚነሱ የዉህደት ጥያቄዎችን ዉድ አደርገዉታል።
በኦፌስል ከሰማያዊ ፓርት ጋር ለመዋሃድ፣ ከአንድነት ፓርቲ በስተቀር ጥያቄ ያቀረበ ድርጅት ስለመኖሩ፣ ብዙ የሚታወቅ ነገር የለም። አቶ ብርሃኑ ተከላ ያሬድ በአሁኑ ወቅት የዉህደት ጥያቄ አቀረቡ የሚሏቸውን ድርጅቶች በተመለከተ «እንደ ፓርቲ መቀጠል ስላልቻሉ ብቻ ድክመታቸውን ወደ ሌላው በማጋባት ህልውናቸውን ለማስቀጠል የሚደረግ ሙከራ የመጠፋፋት ድርጊት እንጂ ውህደት አይደለም» ሲሉም የዉህደት ጥያቄ ያነሱትን ድርጅቶች የዉህደት ጥያቄ ጥሪ አጣጥለዉታል።
በዚህ በዉህደት ዙሪያ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አባላት አመለካከት አንድ እንዳልሆነ የገለጹት አቶ ብርሃኑ፣ «በውህደት ላይ የፓርቲው አመራር አካላት የያዙት አቋም የሁሉም አቋም ላይሆን ቢችልም ሰማያዊ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ እንደመሆኑ መጠን የአብዛኛውን አቋም የማራመድ ግዴታ እንዳለባቸው እንዲሁም ይህንንም ግዴታቸውን በአግባቡ እየተወጡ መሆናቸውን ፓርቲው ያምናል» ሲሉም የሚወሰኑ ዉሳኔዎች ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ መሆኑንም ለማስረዳት ሞክረዋል።
አቶ ብርሃኑ ተከላያሬድ ያቀረቡትን ጽሁፍ እንደሚከተለው አቅርበናል፡
============================================================
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተለያዩ ፓርቲዎች፣ ሚዲያዎች እና ግለሰቦች የሰማያዊ ፓርቲን በውህደት ላይ ያለውን አቋም ሲኮንኑት ይስተዋላል፡፡ ኩነናው ፓርቲው በውህደት ላይ ያለውን አቋም የግለሰብ አቋም ነው እስከ ማለት ይደርሳል፡፡ ስለዚህም የዚህ ጽሑፍ አላማ የፓርቲውን በውህደት ላይ ያለውን አቋም እንዲሁም እውን ፓርቲው በግለሰብ ፖለቲካዊ አቋም የሚመራነውን? የሚለውን ለአንባብያን ለማብራራት እና ለመመለስ ያሰበ ነው፡፡
እኔ እስከማውቀው ፓርቲው በውህደት ላይ ፈጽሞ የተዘጋ አቋም የለውም፡፡ ለዚህም ነው በተለያዩ ጊዜያት ፓርቲው በሚሰጠው መግለጫ ላይ አሁን ባለንበት ሁኔታ ውህደት የሚባል ነገር ቦታ የለውም የሚለው፡፡ ፓርቲ እንደ ፓርቲ የተለያዩ የቤት ስራዎች እንዳሉበት ስለሚያምን እነዚህንም የቤት ስራዎቹን በአግባቡ እና በጥራት ለመስራት ስለሚያስፈልግ ከዚህም ባሻገር ሌሎችም ፓርቲዎችም ከውህደት በፊት በአግባቡ የቤት ስራቸውን መስራት እንደሚኖርባቸውም ከማመን የተነሳ የተያዘ ጊዜያዊ እና ወቅታዊ አቋም መሆኑን ለአንባቢ ማስገንዘብ እፈልጋለሁ፡፡
በሃገራችን የፓርቲ ፖለቲካ ታሪክ ውስጥ የፓርቲዎች የመዋሃድ እና እርስ በእርስ የመበላላት ታሪክ ቢኖርም ዋናው መነሳት ያለበት ነገር ግን ከእነዚህ ታሪኮች ምን ተምረናል የሚለው ጉዳይ ነው፡፡ ታሪክ አሁንም የሚነግረን ከታሪክ የማንማር የታሪክ ቱባ መሆናችንን ነው፡፡ የቅርብ ጊዜ ታሪካችን የሆነው እና የኢትዮጵያን ፖለቲካ ወደ ኋላ የመለሰውን የ1997 ዓ.ም ምርጫ እንደ ማሳያ ሊቀርብ ይችላል፡፡ቅንጅት እንዴት ተቋቋመ? ማን ምን አተረፈ? ማንስ ምን ተጎዳ? ስንት ፓርቲዎች ህይወታቸውን ወይም ህልውናቸውን አጡ? የሚሉት እና የመሳሰሉት ጥያቄዎች በአግባቡ መልስ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡ እነዚህ የትናንት ታሪኮቻችን ፍንትው አድርገው የሚያሳዩን ከፓርቲዎች ውህደት በፊት ምን መሰራት እንዳለበት ነው፡፡
‹‹ወንዙን ስንደርስ እንሻገረዋለን!›› በሚል አስተሳሰብ የሚደረግ ውህደት ወንዙንም ተሻጋሪውንም የሚጎዳ ስለሆነ ፈጽሞ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ ቅንጅት በወቅቱ ባደረገው የወረቀት ውህደት ወንዙ ጋር ሳይደርሱ ተራራው ላይ ሲፈረካከሱ ለማየትተችሏል፡፡ ይህም ሆድን በጎመን ቢደልሉት ልበት በዳገት ይለግማል የሚለውን የሃገራችን ብሂል እንድናስታውስ ያደርጋል፡፡ ከውህደት በፊት ቅድሚያ አንድ በሚያደርጉን ጉዳዮች ላይ አብረን ለመስራት ያለን ተነሳሽነት ምን ያህል እንደሆነ ማስተዋል ይኖርብናል፡፡
እነዚህ ውህደትን የሚያቀነቅኑ ፓርቲዎች ሰማያዊ ፓርቲ እንደ ፓርቲ ባደረጋቸው የተለያዩ እንቅስቃሴዎች እና ዝግጅቶች ላይ ድጋፍ ለማድረግም ሆነ ለመሳተፍ እንዲሁም አብሮ ለመስራት ካደረጉት ጥረት ይልቅ ባይሳካላቸውም እንቅስቃሴዎቹን ለማሳነስ እና ለማጥላላት የተደረጉ ሙከራዎች ይብሱ ነበር፡፡ ከዚህ በፊት ሰማያዊ ፓርቲ ግንቦት 25/2005 ዓ.ም ሰላማዊ ሰልፍ ባካሄደ ጊዜ ሰልፉን በጋራ ከማሳካትና ከመሳተፍ ይልቅ ከአንዳንድ የፓርቲ አመራሮች ሳይቀር እንዴት ተፈቀደላቸው ብለው ገዢውን ፓርቲ ለመውቀስ የዳዳቸውም ነበሩ፡፡
ታዲያ የራሳቸውን የቤት ስራ እንኳን በአግባቡ መስራት የተሳናቸው ፓርቲዎች እንዴት ጣታቸውን ወደ ሰማያዊ ለመቀሰር እንደሚችሉ ፈጽሞ ሊገባኝ የሚችል ጉዳይ አይደለም፡፡ ፖለቲካን ማኪያቶ መጠጫ ያደረጉ ፓርቲዎችም እንኳን ሳይቀሩ ፓርቲው በውህደት ላይ ያለውን ጊዜያዊ አቋም ለመኮነን ሲሞክሩ ማየት አስቂኝም አሳዛኝም ጉዳይ ነው፡፡ የዚህ ጽሑፍ ባለቤት እንደ ግለሰብ ከውህደት በፊት አንድ በሚያደርጉን ነገሮች ላይ ተቀራርበን ለመስራት ፈቃደኛ መሆን ይኖርብናል ብሎ ያምናል፡፡ አንዳንዶች በውስጣቸው ካለው “የብሔር ተዋጽኦ አናሳነት” አንጻር ውህደትን ሲያራግቡ መመልከት የተለመደ ነው፡፡
ሲጀምር አሁንም እንደ አምባገነኑ ኢህአዴግ ከፋፋይ የጎሳ ፖለቲካን ለማስቀጠል ከሚደረግ ሙከራ ተለይቶ አይታይም፡፡ ይህም ደግሞ መጽሐፉ ኢትዮጵያዊ ቀለሙን እንዲሁም ነብር ዥንጉርጉርነቱን ሊቀይር አይቻለውም እንደሚለው ትውልደ ኢህአዴጋውያን በፓርቲዎች ውስጥ አላግባብ ባገኙት ዜግነት የሚያራምዱት እና የሚያቀነቅኑት አስተሳሰብ መሆኑ የሚካድ አይደለም፡፡ ክፍተቶቻችንን በጊዜያዊነት ለመደፋፈን ሲባል የሚደረግ የጥድፊያ ውህደት መጨረሻው አሁን ካለንበት የፖለቲካ አዘቅት ለመውጣት የሚደረግ ትግልን እንዲሁም የህዝብን አመኔታ ለማግኘት የሚደረገውን ጥረት ወደኋላ ሊመልሰው ይችላል ብዬ አምናለሁ፡፡
መቼም እባብ ያየ በልጥ ይበረያል እንደሚባለው ሊሆን ቢችልም እንኳን እንደ ፓርቲ መጠንቀቁ አይከፋም፡፡ በአግባቡ የቤት ስራችንን ሳንሰራ በፍጹም የቤት ስራቸውን በአግባቡ ካልሰሩ ፓርቲዎች ጋር ውህደት መፈፀምም ተገቢ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ቅድሚያ ሁላችንም ያለንበትን በእሾክ የተሞላውን የዴሞክራሲያዊ ፖለቲካ ምህዳር በመጥረጉ አንድ ላይ መስራት ይኖርብናል፡፡ ወንዙን በመሻገር አግዘኝና ይህንን እሰጥሃለው የሚባል ትብብርም ለህወሓት እና ሻዕቢያም እንዲሁም ለህወሓት እና ኦነግም አልበጀም፡፡ ትርፉ በደም እና በስጋ የተሳሰሩ ህዝቦችን በጠላትነት ከማፈራረጅ እና በደም ከማቃባት የዘለለ አልሆነም፡፡
ስለዚህም ትብብራችንም ሆነ ውህደታችን ከጥቅም ተኮርነት እና ጊዜያዊ ሆሆይታ ባሻገር የህዝብን የወደፊት ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ዛሬ ዳቦ ያቋረሰ እና ፈንዲሻ ያስበተነ ውህደት ወይም ትብብር ነገ ሃገር ሊያቋርስ እና ህዝብን ሊበትን ይችላልና ጥንቃቄ ሊወሰድ ይገባል፡፡ ውህደት ማለት የልብ እንጂ የወረቀት መሆን የለበትም፡፡ ሁሉም የቤት ስራውን ሰርቶ ሲጨርስ መሰረታዊ ልዩነቶቹ ላይ በጠረጴዛ ዙሪያ ድርድር በማድረግ ውህደት ለመፈጸም በሩን ከፍቶ የሌሎችን መምጣት ሚጠባበቅ ብቻ ሳይሆን የሌሎችንም የተዘጋ በር በተደጋጋሚ የሚያንኳኳ መሆኑ ግንዛቤ ሊወሰድ ይገባል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በውህደት ላይ ያለውን አቋም የአንድ ግለሰብ አቋም አድርገው በማቅረብ የፓርቲውን እና የአባላቱን ስም ለማጉደፍ የሚደረግ ሙከራ እውነትነት የሌለው ፍሬ አልባ ነገር መሆኑን ለማስረዳት ሰማያዊ ፓርቲ እንዴት እና ለምን ተፈጠረ የሚለውን ብቻ ማየት በቂ ይመስለኛል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ የተቋቋመው ግለሰቦች ከህግ በላይ ሆነው መተዳደሪያ ደንብ እና መርህ እየተጣሰ መቀጠል የለብንም በሚል አቋም ከፓርቲ ጥለው በወጡ ግለሰቦች መሆኑ መዘንጋት የለበትም፡፡ ታዲያ እነዚህ ህግ እንጂ ግለሰብ አይመራንም ያሉ አባላት እንዴት ዛሬ ለግለሰብ አስተሳሰብ ተገዢ ሊሆኑ ይችላሉ ተብሎ ይታሰባል? እዚህ ጋር መዘንጋት የሌለበት ሁሉም የፓርቲ አባላት እንደ ፋብሪካ ውጤት ተመሳሳይ የሆነ አቋም አላቸው ተብሎ ሊወሰድ አይገባም፡፡ከአባላት ውስጥ ውህደትን የሚደግፉ ሊኖሩ ቢችሉም የእነዚህን አባላት አመለካከት ፓርቲው ለፓርቲው ጥቅም ከማሰብ መሆኑን ቢገነዘብም አብዛኛው የፓርቲው አባላት ለውህደት ጊዜው አሁን አይደለም ብለው የሚያምኑ በመሆናቸው የተያዘ አቋም እንጂ የአንድ ግለሰብ አቋም አይደለም፡፡
የፓርቲው ሊቀ-መንበርም ሆኑ የተቀሩት አመራር አካላት አብዛኛው የፓርቲው አባላት የሚያራምዱትን አቋም የራሳቸው ሆነም አልሆነም የማራመድ ግዴታ ያለባቸው መሆኑን የሚያውቁ እንጂ የራሳቸውን ሃሳብ በሌሎች ላይ ለመጫን የሚደረግ ምንም አይነት ሙከራ የለም ብሎ ደፍሮ መናገር ይቻላል፡፡ በውህደት ላይ የፓርቲው አመራር አካላት የያዙት አቋም የሁሉም አቋም ላይሆን ቢችልም ሰማያዊ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ እንደመሆኑ መጠን የአብዛኛውን አቋም የማራመድ ግዴታ እንዳለባቸው እንዲሁም ይህንንም ግዴታቸውን በአግባቡ እየተወጡ መሆናቸውን ፓርቲው ያምናል፡፡
በመጨረሻም ፓርቲዬ ሰማያዊ ውህደት ፈጽሞ አያስፈልግም ብሎ የማያምን እና ከፓርቲዎች ውህደት በፊት ብዙ ስራዎች ሊሰሩ እንደሚገቡ የሚያምን መሆኑ እንዲሁም ሌሎች እንደ ፓርቲ መቀጠል ስላልቻሉ ብቻ ድክመታቸውን ወደ ሌላው በማጋባት ህልውናቸውን ለማስቀጠል የሚደረግ ሙከራ የመጠፋፋት ድርጊት እንጂ ውህደት አይደለም ብሎም ያምናል፡፡በመሆኑም በአሁኑ ሰዓት ከየትኛውም ፓርቲ ጋር አንድ በሚያደርጉን ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ልዩነቶቻችንን ተቻችለን እና ተከባብረን ለመስራት የምንፈልግ እና እየሰራንም የምንገኝ መሆኑን ሊታወቅ ይገባል፡፡ የሆሆይታ ውህደት ከታሰበው ጥንካሬ ይልቅ ድክመትን ሊያመጣ ይችላልና በሰከነ አዕምሮ ቢታይ ይሻላል፡፡ ካልሆነ ግን ከላይ እንዳልኩት ‹‹ሆድን በጎመን ቢደልሉት ጉልበት በዳገት ይለግማል፡፡»

አቡጊዳ

0 comments:

Post a Comment